Monday, 27 June 2011

ተከትዬአለሁ

ተዓምርህን አየን

የምስጋና ቅኔ በፊትህ ለማቅረብ፤
ማለፍ ነበረብን አስፈሪውን ወጀብ።
አንተ ብትረዳን አንተ ብታግዘን፤
ታይተው ነበረ ጠፉ ከመባል አዳንከን።
የትኛው ግብራችን ከሞት አተረፈን፤
ቸርነትህ እንጂ በህይወት ያቆየን።


መንገድ ሰተን ወጥተን ተጋልጠን ለአደጋ፤
ማእበል ወጀብ ገጥሞን እጅግ የሚያሰጋ።
ድንግል ከለለችን ግርማ ሞገስ ሆና፤
ስሟን ጠርተን አንዴም አላፈርንምና።
በመከራው ሰዓት በዚያ ጭንቅ ቦታ፤
ስምሽን ጠረን ድንግል ስምህን ጠራን ጌታ።




ወስብአት ለእግዚአብሄር

Thursday, 23 June 2011

እግዚአብሔር የቅዱሳንን አማላጅነት እንድንጠቀም ጠይቆናል !

5. ሙሴ ስለ እስራኤል ሕዝቦች ያደረገውምልጃ፡ -
- ሕዝቡ የወርቁን ጥጃ አምልከዋልና እግዚአብሔር ሕዝቡን ሊያጠፋ ፈለገ፡፡
- ሊያደርገው የፈቀደውንም ቀጥታ አልፈጸመውም ለወዳጁ ለነቢዩ ሙሴ አማከረው፣ ስለ
ሕዝቡም ያማልድ ዘንድ እድል ሰጠው፣ ሙሴም በእድሉ ተጠቅሞ አማለዳቸው
እግዚአብሔርም ተቀበለው፡፡
- “እግዚአብሔርም ሙሴን፦ ከግብፅ ምድር ያወጣኸው ሕዝብህ ኃጢአት ሠርተዋልና ሂድ፥
ውረድ። ካዘዝኋቸው መንገድ ፈጥነው ፈቀቅ አሉ ቀልጦ የተሠራ የጥጃ ምስል ለራሳቸው
አደረጉ፥ ሰገዱለትም፥ ሠዉለትም። እስራኤል ሆይ፥ እነዚህ ከግብፅ ምድር ያወጡህ አማልክትህ
ናቸው አሉ ሲል ተናገረው። እግዚአብሔርም ሙሴን፦ እኔ ይህን ሕዝብ አየሁት፥ እነሆም
አንገተ ደንዳና ሕዝብ ነው። አሁንም ቍጣዬ እንዲቃጠልባቸው እንዳጠፋቸውም ተወኝ
አንተንም ለታላቅ ሕዝብ አደርግሃለሁ አለው። ሙሴም በእግዚአብሔር በአምላኩ ፊት ጸለየ፥
አለም። አቤቱ፥ ቍጣህ በታላቅ ኃይልና በጽኑ እጅ ከግብፅ ምድር ባወጣኸው በሕዝብህ ላይ ስለ
ምን ተቃጠለ? ግብፃውያንስ። በተራራ መካከል ሊገድላቸው፥ ከምድርም ፊት ሊያጠፋቸው
ለክፋት አወጣቸው ብለው ስለ ምን ይናገራሉ? ከመዓትህ ተመለስ፥ ለሕዝብህም በክፋታቸው
ላይ ራራ። ዘራችሁን እንደ ሰማይ ከዋክብት አበዛለሁ፥ ይህችንም የተናገርኋትን ምድር ሁሉ
ለዘራችሁ እሰጣታለሁ፥ ለዘላለምም ይወርሱአታል ብለህ በራስህ የማልህላቸውን ባሪያዎችህን
አብርሃምንና ይስሐቅን እስራኤልንም አስብ። እግዚአብሔርም በሕዝቡ ላይ ሊያደርግ ስላሰበው
ክፋት ራራ።” ዘፍጥ 32፡7-14፡፡

Wednesday, 22 June 2011

የቅዱሳን አማላጅነት - ስለኛ መጸለይ ነው! እግዚአብሔር የቅዱሳንን አማላጅነት እንድንጠቀም ጠይቆናል !

የቅዱሳን አማላጅነት - ስለኛ መጸለይ ነው!
1. ከጌታችን (እግዚአብሔር) ወልድ ማስታረቅ የተለየ ነው፡፡
2. “… እያንዳንዱ ስለ ሌላው ይጸልይ፤ የጻድቅ ሰው ጸሎት በሥራዋ እጅግ ኃይል ታደርጋለች።” ያዕ 5፡16፡፡
3. ቅዱሳንም ሰዎች ይጸልዩላቸው ዘንድ ጠይቀዋል፡፡ “በቀረውስ፥ ወንድሞች ሆይ፥ የጌታ ቃል እንዲሮጥ በእናንተም ዘንድ
ደግሞ እንደሚሆን እንዲከበር፥ እምነትም ለሁሉ ስለማይሆን ከዓመፀኞችና ከክፉዎች ሰዎች እንድንድን ስለ እኛ ጸልዩ።”
2ኛ ተሰ 3፡1፡፡
4. “ጸልዩልን…” እብ 13፡18፡፡
5. “በጸሎትና በልመናም ሁሉ ዘወትር በመንፈስ ጸልዩ፤ በዚህም አሳብ ስለ ቅዱሳን ሁሉ እየለመናችሁ በመጽናት ሁሉ ትጉ፤
ደግሞ የወንጌልን ምሥጢር በግልጥ እንዳስታውቅ አፌን በመክፈት ቃል ይሰጠኝ ዘንድ ስለ እኔ ለምኑ፡፡” ኤፌ 6፡18-19፡፡
6. ታዲያ እንደኛ ባለ መንፈሳዊ ውጊያ ውስጥ ያሉትን ጸልዩልን ብለን የምንጠይቅ ከሆነ የዚህን ዓለም ውጊያና ፈተና
በድል ተወጥተው የፈጸሙትንና በገነት የሚገኙትን ቅዱሳን ጸልዩልን ብለን መጠየቅ የለብንም???
- “እነርሱ በእምነት መንግሥታትን ድል ነሡ፥ ጽድቅን አደረጉ፥ የተሰጠውን የተስፋ ቃል አገኙ፡፡” እብ 11፡33
- “እኔ ደግሞ ድል እንደ ነሣሁ ከአባቴም ጋር በዙፋኑ ላይ እንደተቀመጥሁ፥ ድል ለነሣው ከእኔ ጋር በዙፋኔ ላይ
ይቀመጥ ዘንድ እሰጠዋለሁ።” ራእይ 3፡21
- “በእሳትም የተቀላቀለውን የብርጭቆ ባሕር የሚመስለውን አየሁ፥ በአውሬውና በምስሉም በስሙም ቍጥር ላይ
ድል ነሥተው የነበሩት የእግዚአብሔርን በገና ይዘው በብርጭቆ ባሕር ላይ ሲቆሙ አየሁ።” ራዕ 15፡2፡፡
እግዚአብሔር የቅዱሳንን አማላጅነት እንድንጠቀም ጠይቆናል !
1. አብርሃምና ንጉሥ አቤሜሌክ፡ ር - “አሁንም የሰውዬውን ሚስት መልስ ነቢይ ነውና፥ ስለ አንተም ይጸልያል፥
ትድናለህም። ባትመልሳት ግን አንተ እንድትሞት ለአንተ የሆነውም ሁሉ እንዲሞት በእርግጥ እወቅ።” ዘፍጥ 20፡7፡፡
2. ኢዮብና ሦስቱ ጓደኞቹ፡- “እግዚአብሔርም ይህን ቃል ለኢዮብ ከተናገረ በኋላ እግዚአብሔር ቴማናዊውን ኤልፋዝን፦
እንደ ባሪያዬ እንደ ኢዮብ ቅንን ነገር ስለ እኔ አልተናገራችሁምና ቍጣዬ በአንተና በሁለቱ ባልንጀሮችህ ላይ ነድዶአል።
አሁን እንግዲህ ሰባት ወይፈኖችና ሰባት አውራ በጎች ይዛችሁ ወደ ባሪያዬ ወደ ኢዮብ ዘንድ ሂዱ፥ የሚቃጠልንም
መሥዋዕት ስለ ራሳችሁ አሳርጉ ባሪያዬም ኢዮብ ስለ እናንተ ይጸልያል፥ እኔም እንደ ስንፍናችሁ እንዳላደርግባችሁ ፊቱን
እቀበላለሁ እንደ ባሪያዬ እንደ ኢዮብ ቅን ነገር ስለ እኔ አልተናገራችሁምና።” ኢዮ 42፡7-8፡፡
3. በሁለቱም ክስተቶች እግዚአብሔር ራሱ የበደሉትን ሰዎች በቀጥታ ተናግሯቸዋል፡ - የኃጢአታቸውንም ሥርየት
በቀጥታ አልሰጣቸውም፡፡ የኃጢአታቸውን ሥርየት እንዲያገኙ ቅዱሳኑ ይጸልዩላቸው ዘንድ ቅድመ ሁኔታ
አስቀመጠላቸው፣ ቅዱሳኑም በሰው ሁሉ ፊት በሁለቱም በደለኞች ፊታቸው ክብር እንዲደገኙ አድርጓል፡፡
4. አብርሃምና ስለ ሰዶም ያቀረበው ምልጃ፡ -
- “እግዚአብሔርም አለ፦ እኔ የማደርገውን ከአብርሃም እሰውራለሁን?” ዘፍጥ 18፡17፡፡
- “አብርሃምም ቀረበ አለም። በውኑ ጻድቁን ከኃጢአተኛ ጋር ታጠፋለህን? ሀምሳ ጻድቃን በከተማይቱ ውስጥ ቢገኙ በውኑ
ሁሉን ታጠፋለህን? ከተማይቱንስ በእርስዋ ስለሚገኙ ሀምሳ ጻድቃን አትምርምን? ይህ ከአንተ ይራቅ ጻድቁን ከኃጢአተኛ
ጋር ትገድል ዘንድ፥ ጻድቁም እንደ ኃጢአተኛ ይሆን ዘንድ፥ እንደዚህ ያለው አድራጎት ከአንተ ይራቅ። የምድር ሁሉ ፈራጅ በቅን
ፍርድ አይፈርድምን? እግዚአብሔርም፦ በሰዶም በከተማይቱ ውስጥ ሀምሳ ጻድቃን ባገኝ ስፍራውን ሁሉ ስለ እነርሱ እምራለሁ
አለ። አብርሃምም መለሰ አለም። እኔ አፈርና አመድ ስሆን ከጌታዬ ጋር እናገር ዘንድ እነሆ አንድ ጊዜ ጀመርሁ ከሀምሳው ጻድቃን
አምስት ቢጐድሉ ከተማይቱን ሁሉ በአምስቱ ምክንያት ታጠፋለህን? ከዚያ አርባ አምስት ባገኝ አላጠፋትም አለ። ደግሞም
ተናገረው፥ እንዲህም አለ፦ ምናልባት ከዚያ አርባ ቢገኙሳ? እርሱም፦ ለአርባው ስል አላደርገውም አለ። እርሱም፦ ጌታዬ አይቆጣ
እኔም እናገራለሁ ምናልባት ከዚያ ሠላሳ ቢገኙሳ? አለ። እርሱም ከዚያ ሰላሳ ባገኝ አላጠፋም አለ። ደግሞም፦ እነሆ፥ ከጌታዬ ጋር
እናገር ዘንድ አንድ ጊዜ ጀመርሁ ምናልባት ከዚያ ሀያ ቢገኙሳ? አለ። እርሱም፦ ከዚያ ሀያ ቢገኙ ስለ ሀያው አላደርገውም አለ።
እርሱም፦ እኔ ደግሞ አንድ ጊዜ ብቻ ብናገር ጌታዬ አይቆጣ ምናልባት ከዚያ አሥር ቢገኙሳ? አለ። እርሱም፦ ስለ አሥሩ አላጠፋትም
አለ።” ዘፍጥ 18፡23-32፡፡
ይቀጥላል...........

Tuesday, 21 June 2011

ዲያስፖራ ዘ ኦርቶዶክስ: የጥፋት ሃይማኖት

ዲያስፖራ ዘ ኦርቶዶክስ: የጥፋት ሃይማኖት

የጥፋት ሃይማኖት

ሃይማኖት በጠባዩ ከፍ ያለ የሞራል ብቃትን የሚያጠይቅ ነው፡፡ በእምነቶች ታሪክ ውስጥ «ብቃት»የሚለው ቃል በተደጋጋሚ የሚነሣ እና ምእመናኑ ሁሉ የሚመኙት ነገር ነው፡፡ እነዚህ ለብቃት የደረሱየየእምነቱ ሰዎች ደግሞ ራሳቸውን ከማሸነፍ አልፈው ዓለምን በፍቅር እና በደግነት ያሸነፉ ናቸው፡፡አንዳንዶቹም ከሰዎችም በላይ ለእንስሳቱ እንኳን ሳይቀር በመራራት ለምነዋል፣ የደግነት ሥራ ሠርተዋል፤ከዚያም አልፎ መከራ ተቀብለዋል፡፡
ሃይማኖት ጸሎትን፣ አምልኮን፣ ደግ ሥራን እና ትምህርትን መሠረት አድርጎ የሰዎችን አስተሳሰብን እናአመለካከትን መለወጥን የሚያመለክት ኃይል ነው፡፡ በሃይማኖት ምክንያት ተደረጉ የሚባሉ ጦርነቶችንእንኳን ጠለቅ እያልን ስናያቸው ሃይማኖትን እንደ መሣሪያ ለመጠቀም በፈለጉ አካላት የተደረጉ እንጂየማይማኖቶችን ድንጋጌ ተከትለው የተደረጉ ሆነው አናገኛቸውም፡፡
አሁን አሁን በዓለማችንም ሆነ በሀገራችን ሃይማኖትን በጥፋት የማካሄድ አዝማሚያዎች እየታዩእየተከናወኑም ነው፡፡ በመግደል፣ ቤተ አምልኮን በማቃጠል፤ ሴቶችን በመድፈር፣ በግዳጅ በማግባት፣መብትን በመንሣት፣ በማስጨነቅ እና በሌላው ቤተ እምነት ላይ ወረራ በማካሄድ ለማሳመን መሞከርእየታየ ነው፡፡
ከዛሬ አምስት ዓመት በፊት በበሻሻ አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ቤተ ክርስቲያን እና በአካባቢው የነበሩክርስቲያኖች እምነታችንን በግድ እንጭናለን በሚሉ ጽንፈኛ «ሙስሊሞች» መታረዳቸው እንኳንከክርስቲያኖች ከሙስሊም ወገኖች እንኳን ከባድ ተቃውሞ ቀርቦበት ነበር፡፡
ከአምስት ዓመታት በኋላ ደግሞ ከሕግም፣ ከታሪክም፣ ከዘመንም የማይማሩ ጽንፈኞች የፕሮቴስታንትአብያተ ጸሎትን እያቃጠሉ እስልምናን በግድ መቀበል አለባችሁ ማለት መጀመራቸውን እየሰማን፤ሰምተንም እያዘንን ነው፡፡
ይህንን የመሰለው ተግባር ማንም ፈጸመው ማንም፤ በማንም ላይ ተፈጸመ በማን ኢትዮጵያ እናኢትዮጵያውያን ፈጽመው ሊቀበሉት እና ዝም ሊሉት የሚገባ ግን አይደለም፡፡
ሰዎች እኛ መልካም ነው ብለን ባመንነው መንገድ እንዲጓዙ መመኘት፣ ለዚህም መትጋት፣ ማስተማር፣በሞራል እና በበጎ ሥራ ልቆ በመገኘት መማረክ፣ ያኛው ተሳስቷል ብሎ ማሰብ እና በሠለጠነ መልኩስሕተት የሚባለውን መግለጥ የቀናዒ ኅሊና ባለቤት መገለጫዎች ናቸው፡፡ ከዚህ ባለፈ ግን «ወደድክምጠላህም የግድ የኔን እምነት ብቻ ትቀበላለህ፣ እምቢ ካልክ ትሞታለህ» በሚል አስተሳሰብ መሥራትከሰውነት ተራ አውጥቶ ወደ ሰይጣንነት የሚያደርስ የሲኦል መንገድ ነው፡፡
ይህ ዓይነቱ አስተሳሰብ ከሦስት ነገሮች ሊመነጭ ይችላል፡፡
የመጀመርያው ሃሳብን ለማስረዳት እና ለማሳመን ዐቅም ሲያጥር ነው፡፡ አንድ ሰው፣ ቡድን፣ተቋም ወይንም ማኅበረሰብ እርሱ በጎ ነው ብሎ የተቀበለውን አስተሳሰብ፣ አመለካከት ወይንም እምነትአስረድቶ፣ አብራርቶ እና በሚገባ አቅርቦ ማሳመን ሲያቅተው የሰነፍ ዱላውን መሠንዘር ይጀምራል፡፡
ይህ ሁኔታ አመለካከት ወይንም አስተሳሰብ እንኳን ሌላውን ሊያሳምን ይቅርና የያዘውም ሰው በሚገባእንዳልገባው ያሳያል፡፡ እርሱም ራሱ ጭፍን ስለሆነ ወይንም ካፈርኩ አይመልሰኝ በሚል እልክ እንደሚከተለው ያመለክታል፡፡ የሃሳብ ክርክር ከተነሣ ልሸነፍ እችላለሁ፣ ሊያሳምነኝ ይችል ይሆናል ብሎየሚሰጋ አካል ከሃሳብ ክርክር ይልቅ የመሣርያውን ክርክር ይመርጣል፡፡ ምክንያቱም የመሣርያ ክርከርከሃሳብ ክርክር ይልቅ ቀላል ነውና፡፡
ሁለተኛው ምክንያት ደግሞ ከውጤቱ ይልቅ ድርጊቱን ብቻ በማየት የሚመጣም ነው፡ በዓለምላይ ያሉ እምነቶች ሁሉ በአንድ ዓላማ ይስማማሉ፡፡ ሰውን ከክፉው አውጥተው ወደ በጎው ዓለምመውሰድ ዓላማቸው ነው፡፡ ይህም ማለት ዋና አጀንዳቸው ሰው ነው ማለት ነው፡፡ ታድያ ልታሳምነው እናልታድነው የሚገባውን ሰው እንዴት ገድለህ ታሳምነዋለህ? ከገደሉ በኋላ ማሳመንስ አለ?
ይህ ዓይነቱ ሰይጣናዊ ሥራ የሚሠራው የመሰላቸውን ነገር ማድረጋቸውን እንጂ የሚያመጡትን ውጤትምንነት በማያስቡ ጨለምተኞች ነው፡፡ ጨለምተኞች ለራሳቸው ጀብዱ እንጂ ለሚያስከትሉት ውጤትአይጨነቁም፡፡ የፈለጉትን እና መልካም መስሎ የታያቸውን ማድረጋቸውን እንጂ በድርጊታቸው ምንለውጥ እንዳመጡ ማሰብ አይፈልጉምም፤ አይችሉምም፡፡
ሦስተኛው ምክንያት ደግሞ ከእምነት ውስጥ «ሰውነት» ሲጎድል የሚከሰት ነው፡፡ ማንኛውምአማኝ አማኝ ከመሆኑ በፊት ሰው ነበር፡፡ ለማመን የበቃውም ሰው በመሆኑ ነው፡፡ ግኡዝ ወይንም እንስሳቢሆን ኖሮ አያምንም ነበር፡፡ አማኝ መሆኑ ሰው በመሆኑ ሊኖሩት የሚገቡትን በጎ ነገሮች ይበልጥያጠናክራል፤ ሌሎች በጎ ነገሮችንም ይጨም ርባቸዋል፤ ሰው በመሆኑ የሚከሰትበትን ድካምም በእምነትያሸንፈዋል፡፡
አማኝነት ሰው መሆንን ካጠፋ እና አውሬነትን ከተካ ግን ይህ አማኝነት አይሆንም፡፡ ምክንያቱም አራዊትሃይማኖት የላቸውም፤ ሊኖራቸውም አይችልምና፡፡ ለምሳሌ ለሰዎች ማዘን ሰው የመሆን ጠባይ ነው፡፡ለዚህም ነው በሁሉም ዓይነት ማኅበረሰቦች ውስጥ ሰዎች ሲሞቱ በልዩ ሁኔታ የሚታዘንላቸው፡፡ ይህንንጠባይ እምነት ያጠነክረዋል፤ በሚገባ ጎልቶ ወጥቶ ለምግባር እንዲበቃ ያደርገዋል እንጂ ሊያጠፋውአይገባም፡፡
ሰውን በመግደል፣ የሰውን ቤተ እምነት በማቃጠል፣ የሰውን ክብር በመንካት፣ መብቱን በመገደብ፣በእምነቱ ምክንያት አድልዎ በማድረግ፣ በማስጨነቅ እና አካላዊ ጉዳት በማድረስ ለማሳመን ወይንምለማጥፋት መጣር በምንም መልኩ የአማኝ ሰው መገለጫ ሊሆን አይችልም፡፡ እምነት ሰውነትንአይደፈጥጥምና፡፡
አሁን አሁን እምነታቸው ሰውነታቸውን ያጠፋባቸው፤ በእምነት ኃይል ከሰውነት ወደ መልአክነትይሸጋገራሉ ሲባሉ ጭራሽ ወደ አውሬነት የወረዱ አካላትን እያየን ነው፡፡ የአውሬን ሥራ ለመሥራትእምነት ምን ያደርጋል) እምነትኮ አውሬነትን አሸንፎ፣ ሰውነትን አልዕሎ መልአክነትን ገንዘብ ለማድረግነው፡፡
ሰውን በእምነቱ ምክንያት መግደል፤ ገንዘቡን መስረቅ፣ ሰውን በእምነቱ ምክንያት መጨቆን፤ ሴትንበእምነቷ ምክንያት መድፈር፤ ድኻን በእምነቱ ምክንያት አለ መርዳት፣ የሰውን ቤት በእምነቱ ምክንያትማቃጠል እንዴት ሃይማኖት ሊሆን ይችላል? «መግደል፣ መስረቅ፣ መድፈር፣ አድልዎ፣ ማቃጠል»እነዚህን ድል መንሣት የተሣነው እምነት እንዴት እምነት ይሆናል?
ይህ ሰይጣናዊ ተግባር በማንም ተፈጸመ በማን፣ በማንም ላይ ተፈጸመ በማንም ላይ በሁሉም የሰው ዘርሊወገዝ የሚገባው ድርጊት ነው፡፡ ምክንያቱም ከሰውነትም የወረደ ድርጊት ስለሆነ፡፡ ይህ ዓይነቱ ድርጊትሰዎችን አይወክልም፣ አማኞችንማ ጭራሽ አይመለከትም፡፡ ይህ ዓይነቱን ሰይጣናዊ ሥራ እምነት አለኝየሚል ሁሉ ሊያወግዘው፣ ሊጸየፈው እና ሊያነውረው የሚገባ ነው፡፡
ትናንት በኦርቶዶክሳውያን ላይ፣ ዛሬ ደግሞ በፕሮቴስታንት ወገኖቻችን ላይ ተፈጸመ፡፡ ነገ በሌሎች ላይለሦስተኛ ጊዜ እስኪፈጸም መጠበቅ የለብንም፡፡ በኔ አልተፈጸመም፣ እኔንም አይመለከትም ልንልምአንችልም፡፡ ይህ ዓይነቱ ድርጊት በአንድ እምነት ላይ የሚፈጸም ሳይሆን «በሰውነት» ሰው በመሆን ላይየሚፈጸም ወንጀል ነው፡፡ ሌላው ቀርቶ ይህንን የፈጸሙት ወገኖች እንኳን ይህንኑ አስተሳሰባቸውንበአስተሳሰብ ልዕልና እንዲለውጡ እንጂ በገጀራ እንዲለውጡ ማናችንም አንፈልግም፡፡
የድኅነት እንጂ የጥፋት ሃይማኖት ሊኖር አይችልምና፡፡

Saturday, 11 June 2011

ድንጋይ ስድብ ነው ወይ


አንዳንድ ጊዜ በተለምዶ የተቀበልናቸው፤ እኛም ሳንመረምር ዝም ብለን የምናደርጋቸው እና የምንናገራቸው ነገሮች፣ የያዙት እውነታ ከሚታወቀው በተቃራኒ ሆኖ የሚገኝበት ጊዜ አለ፡፡ ትምህርት የማይገባውን፣ ሰነፉን እና ደደቡን፣ ሥራ ጠሉን እና ዘረጦውን ለመግለጥ «እገሌ ድንጋይ ነው» እንላለን፡፡ የሌላውን ሀገር አላውቅም እንጂ ኢትዮጵያ ውስጥ ግን እንዲያ ብሎ መሳደብ እና ድንጋይን ለውጥ ለሌለው፣ ለሰነፍ እና ለሥራ ጠል አእምሮ ምሳሌ ማድረግ የምንችል አይመስለኝም፡፡

ስለ ኢትዮጵያ ፊደል አመጣጥ ሊጠየቅ የሚችለው መረጃ ድንጋይ ነው፡፡ ቀደምት ሳባውያን ታሪካቸውን እና የጉዞ ዘገባቸውን፣ ንግግራቸውን እና እምነታቸውን ጽፈው ያስቀመጡት በድንጋይ ላይ ነው፡፡ ኢትዮጵያ ውስጥ ዛሬ የምንጠቀምበት እና የምንኮራበት ፊደል እንዴት እና ከየት ተገኘ ብለን ብን መረምር የመረጃው ባለቤት ድንጋይ ነው፡፡ ፊደላችንን ብቻ ሳይሆን በወቅቱ የነበሩትን የጥበብ መሣርያዎቻችንን፣ የጦር መሣርያዎቻችንን፣ የእህል ዓይነቶቻችንን ፣ የምንጠቀምባቸውን ከብቶች፣ የዛፎቻችንን እና የማዕድናት ሀብቶቻችንን እንኳን የምናገኘው ከድንጋይ ላይ መረጃዎቻችን ነው፡፡

የኢትዮጵያ የጥንቱ ግዛት ከየት ተነሥቶ የት ይደርስ እንደ ነበር፣ ማን ማን የተባሉ ሕዝቦች በአኩስም መንግሥት ሥር ይተዳደሩ እንደ ነበር፣ የትኞቹ ቦታዎች በጦርነት ገብረው እንደ ነበር፣ የትኞቹ ቦታዎች ወርቅ፣ የትኞቹስ ቦታዎች አልማዝ፣ የትኞቹስ ቦታዎች ዕንቁ ይገብሩ እንደ ነበር የጥንቱን መረጃ የያዘው የድንጋይ ላይ ጽሑፍ ነው፡፡

ለመሆኑ የኢትዮጵያን የብዙ ሺ ዓመታት ታሪክ የድንጋይ ያህል አሟልቶ የሚያውቀው አለ? ለቅድመ ጽሑፍ ታሪካችን ምስክሩ የአኩስም እና የደቡብ ትክል ድንጋዮች ናቸው፤ ለአኩስም ዘመን ታሪካችን ምስክሩ በአኩስም አካባቢ እና ባሕር ተሻግሮ በየመን የተገኙት የድንጋይ ጽሑፎች ናቸው፡፡ በዘመኑ የተጻፈ የታሪክ መረጃ የለም ተብሎ በባለ ታሪኮች ዘንድ «የጨለማ ዘመን» እየተባለ ስሙ የጠፋው የዛግዌ ሥርወ መንግሥት ታሪካችን እንኳን ሕያው ምስክሩ የድንጋይ ውቅር አብያተ ክርስቲያናት ናቸው፣ ከዛግዌ ሥርወ መንግሥት በኋላ ለመጣው የመካከለኛው ዘመን ታሪካችንም ከጦርነት የተረፉን መረጃዎቻችን በየዋሻዎቹ የምናገኛቸው መዛግብቶቻችን ናቸው፤ የጎንደር ዘመንም አሻራዎቹ ከድንጋይ የተሠሩት ግንቦቻችን ናቸው፡፡ ሐረር ለነበረው ሥልጣኔ እና ታሪክ ሕያው ምስክራችን ከድንጋይ የተሠራው የሐረር ግንብ ነው፡፡ እናም ሦስት ሺም እንበለው ሰባት ሺ የኛን ታሪክ ከድንጋይ በተሻለ ማን ያውቀዋል፡፡

በአሥራ ስድስተኛው መቶ ክፍለ ዘመን የነበረውን የክርስቲያን ሙስሊም ጦርነት በተመለከተ እንኳን በሁለቱም ወገን ከተጻፉት ታሪኮች ሌላ ምስክር የምናገኘው በድንጋይ ላይ ነው፡፡ የት የት ቦታዎች ጦርነቱ ተደረገ? በወቅቱ የድል በለስ እየቀናው የመጣው የኢብን ኢብራሂም አሕመድ አልጋዚ ወታደሮች እና ተከታዮች የት ቦታ ላይ ተቀበሩ? በመጨረሻም አሕመድ አልጋዚ የት ቦታ ድል ሆነ? እያልን ብንጠይቅ በወቅቱ የነበረውን ታሪክ የምናገኘው «የግራኝ» ድንጋይ በመባል ከሚታወቁት እና በወቅቱ ከተተከሉት ትክል ድንጋዮች ይመስለኛል፡፡

ሀገራችን በጦርነት ስተታመስ፤ ሕዝቦቿም ራሳቸውን እና ሀገራቸውን ሲከላከሉ የኖሩ ናቸው፡፡ አብዛኛው ታሪካችንም የጦርነት ታሪክ ነው ይባላል፡፡ በዚህም የተነሣ አያሌ ታሪካዊ መዛግብትን አጥተናል፡፡ መጻሕፍቱ፣ ሥዕላቱ፣ ደብዳቤዎቹ፣ ንዋያቱ እና የወግ ዕቃዎቹ እየተቃጠሉም፣ እየተዘረፉም፣ በአፈር እየተበሉም አልቀውብናል፡፡ የተረፉትም ቢሆኑ እድሜ ለድንጋይ በየዋሻዎቹ ተደብቀው፣ ከአፈር መበላት እና ከእሳት፣ ብሎም ከቀበኛ የተረፉልን ናቸው፡፡ እነዚህ የድንጋይ ምሶሶ እና የድንጋይ ወጋግራ ዘርግተው የተፈጠሩ የድንጋይ ዋሻዎች ባይኖሩ ኖሮ፣ አሁን የምንኮራባቸውን የብራና መጻሕፍት፣ ንዋያት እና የወግ እቃዎች አጥተን ተረት ብቻ ወርሰን በቀረን ነበር፡፡

እነዚያ የድንጋይ ዋሻዎች ንብረቶቻችንን ብቻ ሳይሆን በእነዚያ የጦርነት እና የመከራ ጊዜያት እናቶቻችንን እና አባቶቻችንንም አስጠልለው አትርፈዋል፡፡ በሰሜን ሸዋ ተራሮች ሥር የሚገኙት እና «ዋሻ እገሌ» እየተባሉ የሚጠሩት ለቁጥር የሚታክቱት ዋሻዎቻችን፣ የባሌው ሰብስቤ ዋሻ እና የጋሞጎፋው የቦረዳ ዋሻ ለዚህ ምስክሮ ቻችን ናቸው፡፡

ቀደምቶቻችን ሰማይ ሰማዩን ብቻ ሲያዩ አልኖሩም፡፡ ምድር ንም በሚገባ ዐውቀዋት ነበር፡፡ ከሰሜን እስከ ደቡብ የምናገኛቸውን የድንጋይ ጥበቦቻችን የተሠሩባቸው ዐለቶች ተመሳሳይ ጠባይ ያላቸው ናቸው፡፡ እነዚያ ጠቢባን ድንጋዮቹን በሁለት መመዘኛ ነው ሲመርጧቸው የኖሩት፡፡ ቅርጽ ለማውጣት የሚያስችል እና ረዥም ዘመን ለመኖር ዐቅም ያለው፡፡ በሁለቱም ተሳክቶላቸዋል፡፡ የሚገርመው ግን እነዚህን መመዘኛዎች የሚያሟላውን ድንጋይ ለማወቅ የሚጠይቀውን የጂኦሎጂ ዕውቀት ከየት አገኙት? የሚለው ነው፡፡

አንድ ሊቅ «ኢትዮጵያውያን ማለት ድንጋይ ሲያናግሩ የኖሩ ሕዝቦች ናቸው» በማለት የተናገረው እውነቱን መሆን አለበት፡፡ መሬቱን ፈልገው፣ ድንጋዩን አጥንተው፣ መርጠው እና አለዝበው ዘመናትን የሚሻገር የሥልጣኔ አሻራ መተው የቻሉት ድንጋይ የማናገር ችሎታ ስለነበራቸው መሆን አለበት፡፡ እነዚያን ድንጋዮች ቤት ብቻ አይደለም የሠሩባቸው፡፡ መሠዊያቸውን፣ መስቀሎቻቸውን እና ደወሎቻቸውንም ሠርተውባቸዋል፡፡ በወሎ፣ በጎንደር እና በጣና ገዳማት የምናገኛቸው የድንጋይ ደውሎች ድምፃቸው ከመዳብ እና ከብረት ደውሎች ይበልጣል፡፡ ለዚህ የተስማማውን፣ ድምፅ ሊያወጣ የሚችለውን የድንጋይ ዓይነት በምን ዐወቁት? ወይስ ያን ጊዜ የጂኦሎጂ ትምህርት ነበረ እንዴ?

ምናልባትም ቀደምቶቻችን የተፈተነ ሕይወትን የሚወድዱ ሳይሆኑ አይቀሩም፡፡ በቀላሉ ከእንጨት፣ሣር እና ቅጠላ ቅጠል ሊሠሯቸው ይችሉ የነበሩትን ነገሮች ከባድ ከሆነው እና ልዩ ችሎታን እና ቴክኖሎጂ ከሚጠይቀው ከድንጋይ ለመሥራት የፈለጉት ተፈጥሮን ለመፈተን፣ ዕውቀትንም ለመገዳደር ይመስለኛል፡፡ የጀግንነታቸው አንዱ መገለጫም ጠላትን በመቋቋም ብቻ ሳይሆን ተፈጥሮን ተፈታትነው በማስገበርም ጭምር እንዲሆን ሳያስቡ አልቀሩም፡፡ በዚህ መልኩ መከራን ተቋቁሞ ማለፍን አስቀድመው ከተፈጥሮ ጋር ባደረጉት ትግል ስለ ለመዱት ሳይሆን አይቀርም እነዚያን ክፉ ጊዜያት ታሪክ እና ቅርስን ጠብቀው ለማሳለፍ የቻሉት፡፡

ክርስቲያንም ሙስሊምም ያልነበሩት ቀደምት የዳአማት መንግሥታት ታሪካቸውን ያቆዩት በድንጋይ ነው፣ በክርስትናቸው የታወቁት የዛግዌ ነገሥታት እና ሕዝቦችም ታሪካቸውን ያቆዩት በድንጋይ ነው፡፡ ሙስሊም የተነበሩት ግዛቶቻችን እና ሕዝቦችም ታሪካቸውን ያቆዩት በድንጋይ ላይ ነው፡፡ በትግራይ፣ በላስታ እና በጎንደር ከ3000 በላይ ውቅር አብያተ ክርስቲያናትን እናገኛለን፡፡ በአርጎባ «ራሳ» አካባቢ ደግሞ አርጎባዎች «ቱሉል» ብለው የሚጠሯቸው ወደ 3000 የሚጠጉ በባለሞያ የተቀረጹ የድንጋይ ምስሎች እናገኛለን፡፡ እናም፣ ምንም በሃይማኖት ብንለያይም ሥልጣኔያችን ግን በድንጋይ ላይ ሠፍሮ አንድነታችንን ይመሰክርብናል፡፡

ከሰሜን እስከ ደቡብ ያለውን የኢትዮጵያውያንን አንድነትስ ቢሆን ከድንጋይ በተሻለ ማን ይመሰክረዋል፡፡ አንድ ሰው እንዳ ለው «እስክስታ እና ድንጋይን ያህል የኢትዮጵያን ሕዝቦች አንድነት የሚያሳይ ባሕላዊ ገጽታ የለም»፡፡ ትግራይ ላይ ከወደ አንገት እና ትከሻ የጀመረው እስክስታ፣ አገው እና አማራ ላይ ሲደርስ አንገትን ከትከሻ ያያይዝና፤ ኦሮሚያ ላይ አንገትን፣ ትከሻን እና ወገብን ከእጅ እንቅስቃሴ ጋር ያዛምዳል፡፡ ወላይታ እና ሐድያ ላይ ሲወርድ ደግሞ ወገብን ታክኮ ወደ ዳሌ ዝቅ ይላል፡፡ ከዚያም ደቡብ ጫፍ ሐመሮች ላይ ሲገባ እስክስታው በእግር ይጨርሳል፡፡ ያኔም ኢትዮጵያ አንድ ሰው ሆና ትታያለች ማለት ነው፡፡

ድንጋይም እንዲሁ ነው፡፡ ከሰሜን አኩስም እስከ ባሌ ተራሮች፣ ከምዕራብ ኦጋዴን እስከ አሶሳ፣ ኢትዮጵያ በታሪካዊ የድንጋይ ሐውልቶች የተሞላች ናት፡፡ በጣም የሚገርመው ደግሞ እነዚህ የድንጋይ ሐውልቶች ከመቃብር እና ከታሪካዊ ሁነቶች ጋር የተያያዙ መሆናቸው ነው፡፡

የአኩስም ሐውልት በታላላቅ የአኩስም ነገሥታት መቃብር ላይ መታሰቢያ ሆኖ ቆሟል፡፡ ከአዲስ አበባ ደቡብ 50 ኪሎ ሜትር ርቀት ጀምሮ በሲዳማ፣ ወላይታ፣ ሐድያ፣ ስልጤ፣ ከምባታ፣ በሰሜን በአዋሳ ሐይቅ፣ በምዕራብ ደግሞ በአባያ ሐይቅ ተከብቦ የሚገኘውና ከ150 በላይ ታሪካዊ ሥፍራዎችን የያዘው የድንጋይ ሐውልቶች ስብስብ፣ እንደ ሰሜኑ ሁሉ የመቃብር ሥፍራዎችን እና ታሪካዊ ሁነቶችን መሠረት ያደረገ ነው፡፡ በኦሮሚያ ክልል በተለይም በአርሲ እና ባሌ የምናገኛቸው ሐውልቶችም ይህንኑ የሰሜን እና ደቡብ እሴት ተጋርተው፣ አንድነታችንንም መስክረው ይሄው ዛሬም ይታያሉ፡፡

ድንጋይ ሥልጣኔያችንን ብቻ ሳይሆን ጀግንነታችንንም ሲመሰክር የኖረ ነው፡፡ መሣርያ እንደ ልብ ባልነበረበት በዚያ ዘመን ሉዓላዊነታችን ታፍሮ፣ ድንበራችን ተከብሮ፣ የኖረው በድንጋይ ጭምር ነው፡፡ ቆንጥር ለቆንጥር መወርወር፣ ተራራ ለተራራ መኖር የለመደው ሐበሻ በተራሮች ጫፍ መሽጎ ይለቅቀው በነበረው ናዳ ያለቀውን ጠላት ያህል ሌላው መሣርያችን መጨረሱን እጠራጠራለሁ፡፡ ከሜዳማ አካባቢዎች ይመጡ የነበሩት አብዛኞቹ የውጭ ጠላቶች ከመሣርያችን በላይ መቋቋም ያቃታቸው ለሀገሩ ልጅ ብቻ ይበገር የነበረውን መልክዐ ምድራችንን ነው፡፡

እናም ድንጋይ የታሪካችን፣ የፊደላችን፣ የሥልጣኔያችን፣ የእምነታችን፣ የቀጣይነታችን፣ የአንድነታችን፣ የኅብራችን መገለጫ ከሆነ «ድንጋይ» እንዴት ስድብ ይሆናል?

Friday, 3 June 2011

ዲያስፖራ ዘ ኦርቶዶክስ: ሊነበብ የሚገባ ጽሁፍ,, ተዋህዶን ታድሷት ዘንድ የተዘጋጃችሁ እናንት እንማን ናችሁ ?

http://ahatitewahedoorthodox.blogspot.com/

ዲያስፖራ ዘ ኦርቶዶክስ: ሊነበብ የሚገባ ጽሁፍ,, ተዋህዶን ታድሷት ዘንድ የተዘጋጃችሁ እናንት እንማን ናችሁ ?

ዲያስፖራ ዘ ኦርቶዶክስ: ሊነበብ የሚገባ ጽሁፍ,, ተዋህዶን ታድሷት ዘንድ የተዘጋጃችሁ እናንት እንማን ናችሁ ?

ሊነበብ የሚገባ ጽሁፍ,, ተዋህዶን ታድሷት ዘንድ የተዘጋጃችሁ እናንት እንማን ናችሁ ?


ክብር የሚገባህ አምላካችን እግዚአብሄር ሆይ ፦ የአለማት ሁሉ አስገኝ ፣ የፍጥረታት ሁሉ ጌታ ፤ እኔ ልጅህ እንዳልል የአባትነት ክብርን ያልሰጠሁህ ፣ እኔ ባሪያህ እንዳልል የጌትነት ትእዛዝህን ያልፈፀምኩ ለምንም የማልጠቅም የወደቅሁ ሰው ስሆን አሁን ግን እንደ አዋቂ ፣ ጥበብን ገንዘብ እንዳደረገ በደምህ ስለዋጃሃት ቤተ-ክርስቲያን በድፍረት እናገር ዘንድ ራሴን አዘጋጅቻለሁና ማስተዋሉ አቅቶኝ ፍቅሩ ጎድሎኝ አንተን የሚያሳዝን ቃላትንና ሃረጋትን ብጠቀም ስለ ተወዳጇ እናትህ ስለ ቅድስት ድንግል ማርያም ብለህ ይቅርታህን እንድትሰጠኝ እለምንሃለሁ፡፡ አምላክ ሆይ አንተ በእውነት ምስጋና ይገባሃል፡፡

ይህን ፅሁፍ ሳዘጋጅ አሁን ካየሁበት አተያይ አልፌ ከተለያዩ አቅጣጫወች ማየት የሚገቡኝ ፣ ነገር ግን ከእኔ የተሻሉ ሰወች እንዲያዩት በማለት ያለፍኳቸው ጉዳዮች ቢኖሩም ይህን ፅሁፍ ግን ሊያሳጥረው አልቻለም፡፡የሆነው ሆኖ አሁን ያየሁበት አተያይም ቢሆን ሊፅፉት የሚገቡት በቤተ-ክርስቲያናችን ያሉ ሊቃውንት ይሆኑ ዘንድ እንዲገባም አምናለሁ፡፡ደግሞም የክርስቶስን በጎች ይጠብቁ ዘንድ ክርስቶስ አደራ ያላቸው የቤተ-ክርስቲያን እረኞች በክርስቶስ ጥበብ እየተመላለሱ ህዝቡን ሁሉ በመልካም ማሰማሪያ የሚያሰማሩቱ ፦ ስለ ወቅቱ እንቅስቃሴና መዘዝ የሚገባውን እርምጃ እየወሰዱ እንደሆነ እንኳን ባምንም ፣ ከእረኞች ወገን ያልሆንኩት እኔ ፣ ለዚያውም ገራም ካልሆኑት አስቸጋሪ በጎች መካከል የምመደብ ፣ በዚህ ተግባሬ የእውነተኞቹን እረኞች ስራ እቃወም የሆንን እያልኩ እፈራለሁ፡፡የሆነ ሆኖ ቤተ-ክርስቲያን ማለት እናት ማለት ስለሆነ እኔም እንደ ቤተ-ክርስቲያን ልጅነቴ መከራዋንና ፈተናዋን ዝም ብየ አይ ዘንድ የሚገባ ስላልሆነ ይህን ፅፍኩ፡፡

ቤተ-ክርስቲያን ተሃድሶ ያስፈልጋታል የሚሉትን አዳሾች ከመሞገቴ አስቀድሞ ተሃድሶ የለም ፣ ሰነፎች የፈጠሩት የሃሰት ወሬ ነው የሚሉትን ጥያቄ ልጠይቃቸው፡፡ እናንተ ተሃድሶ የለም የምትሉ ወንድሞቼና እህቶቼ በተለይም በ40 ና በ80 ቀን በስላሴ ስም የተጠመቃችሁ ፣ እናንተ በክርስቶስ የባህርይ አምላክነት የምታምኑ ፣ የድንግል ማርያም ፍቅር በልቦናችሁ የሚቃጠል ፣ የቅዱሳን የሰማእታት ወዳጆች ፣ የተዋህዶ ቤተ-ክርስቲያናችሁ ህግና ስርአት ውበት ጌጣችሁ የሆነላችሁ፤ እስኪ መልሱልኝ ፦የዲያቢሎስን የጥፋት አሰራር የክፋቱንም ጥበብ እረሳችሁት? የቀደመውስ እባብ የመጨረሻው ቀን እንደደረሰ አውቆ ዝናሩን በቤተ-ክርስቲያን ላይ እያርከፈከፈ እንደሆነ አላስተዋላችሁም? ወይንስ ዲያቢሎስ መልካም የሆነውን መንፈሳዊ እሴት ይሰርቅ ዘንድ የሚተጋ ሌባ እንደሆነ ዘነጋችሁ? አለዚያስ ተዋህዶ ቤተ-ክርስቲያናችሁ የመንፈሳዊ ፀጋ ባለሃብት እንደሆነች አታምኑም? ክርስቲያኖች፦ ተዋህዶ ቤተ-ክርስቲያናችሁ በዚህ ጊዜ ያለች ብቸኛ በእግዚአብሄር ደም የተዋጀች ፣ መሰረቷና ጉልላቷ ክርስቶስ የሆነላት ፣ ዘወትርም በቅዱሳን ፀሎት የምትጠበቅ ፣ ዶግማና ቀኖናዋም ሰማያዊ እንደሆነ ካመናችሁ ዲያቢሎስ ይህን ሁሉ እየተመለከተ ዝም የሚል ይመስላችኅል? የዲያቢሎስስ ተግባር መልካሙን ሁሉ ለክፋት ማስገዛት እንደሆነ ትዘነጋላችሁ? እንግዲህስ ዲያቢሎስ ሌባ እንደሆነ ሌባም ሊሰርቅ ወርቅና ብር ካለበት ከሃብታም ግቢ ይገባ ዘንድ ይፋጠናል እንጂ የደሃ ቤትን እንዳይሰረስር ቤተ-ክርስቲያንም በአለም ያለች የሰማያዊ ፀጋ ባለሃብት እንደሆነች ካወቅን ወርቅና ብር ተከማችቶ የሚቀመጥበትን ነቅቶ ከሌባ እንደማይጠብቅ ሰነፍ ሰራተኛ እንሆን ዘንድ የተገባ ነውን? እንግዲህ አንዘነጋ ፣ የዲያቢሎስ ፈተናወችና መከራወች በየወቅቱ ልዩ ልዩ መሆናቸውን ተገንዝበው ፤ በአለም ሳላችሁ መከራ አለባችሁ የተባለው አማናዊ ቃል ይፈፀም ዘንድ የእግዚአብሄር የሆኑቱ ዘወትር በመከራ ይፈተናሉ፡፡ ያለ መከራም አክሊል ይገኝ ዘንድ አይቻልምና ፈተናውን ሁሉ በጥበብና በትእግስት የሚያሳልፉቱ ቅዱሳን ደግሞ በመከራቸው እንዲመኩ እናውቃለን፡፡ ታዲያ እንደዚህ ከሆነ የተሃድሶን ነገር እንደምን አላወቃችሁም? በህንድ ፣ በአርመን ፣ በሶሪያ ፣ በግብፅ ና በኤርትራ የተደረገውን አልተማራችሁም? ወይንስ አለማወቅን እውቀት አድርጋችሁ ተቀምጣችኅል? ወይንስ ተሃድሶ የሚለውን ስያሜ የፕሮቴስታንቶች ተንኮል በኦርቶዶክስ ቤተ-ክርስቲያን ላይ በሚለው ቢተካ ልባችሁ ይገኝ ይሆን? ወይንስ በተሃድሶ ሴራ ውስጥ ተባባሪ ሆናችሁን? እኔ ግን ርቃችሁ እንደሆነ እፈራለሁ ፦ የዚህ አለም ፍቅር ወይስ ጣጣ ከእግዚአብሄር እቅፍ አወጣችሁ? ከቤተ-ክርስቲያናችሁስ የእጣን ሽታ የአለም የክርፋቷ ጣእም በለጠባችሁ? እንግዲህ ተመለሱ ፤ ወደ እናታችሁ ጉያ ግቡና ታቀፉ ፤ ቤተ-ክርስቲያን እናታችሁ ናትና በደስታዋም በመከራዋም ከጎኗ አትለዩ ፤ በወቅት የማይገኝ የሩቅ ዘመድም አትሁኑ ፤ ቅረቧት ክበቧት ዘወትርም ፊቷን ተመልከቱ ፤ ያለቀሰች እንደሆነ አብራችሁ እያለቀሳችሁ እንባዋን ታብሱላታላችሁ ፤ አዝና ከሆነ ከጎኗ ሆናችሁ ሃዘኗን ትጋራላችሁ ፤ ብርድና ቁር ቢፈራረቁባት ፣ ረሃብና ጥማት ቢያደክማት ጉልበተኛ ቢበረታባት ደጀን አለኝታ ትሆኑላታላችሁ፡፡ እንዲህ ተብሎ እንደተፃፈ ፦ፅዮንን ክበቧት በዙሪያዋም ተመላለሱ፡፡ እንግዲህ በዚህ ዘመንም በቤተ-ክርስቲያን ላይ የደረሰው መከራ በረከሰው፣ በተወገዘውና በከረፋው የምንፍቅና አስተምሮ ታጅለው ጥንታዊቷን እምነት ሊያድሱ የተነሱ ደፋር ተሃድሶወች እንደሆኑ ልብ እንበል ፡፡ እነዚህ በቤተ-ክርስቲያን ቅጥር ያሉ ፣ በቤተ-ክርስቲያን ማእድ የሚመገቡ ፤ ነገር ግን ሆዳቸው አምላካቸው ፣ ሃሳባቸው ምድራዊ ፣ የዲያቢሎስ ባርያወች የሆኑ ተዋህዶን እናድስ ብለው በዲያቢሎስ ጥበብ ተነስተዋልና ሃገራችን በሰማይ የሆን እኛ የቀደሙ አባቶቻችንን ደጀን አድርገን በክርስቶስ ጥበብ እንረታቸው ዘንድ ይገባል፡፡ ስለዚህ እናንተ ወንድሞቼና እህቶቼ በትክክለኛይቱ ቤተ-ክርስቲያን ላይ መከራ እንደመጣ ፣ መምጣቱም ግድ እንደሆነ ካመናችሁ ፦ መከራው ምን እንደሆነ ቀርባችሁ ተማሩ ፤ ሰውንም ከማድነቅና ከማገልገል እግዚአብሄርን እናገለግል ዘንድ ለቤተ-ክርስቲያናችንም ዘብ እንቆም ዘንድ እንትጋ፡፡ እንዲህም እንድናደርግ አምላካችን እግዚአብሄር ይርዳን፡፡

እናንተ ግን ተዋህዶን ልታድሱ የተነሳችሁ አዳሾች ፦ ተዋህዶን ታድሱ ዘንድ ምን ህፀፅ ጉድለት አገኛችሁባት? የትኛውንስ የሃይማኖት ዶግማ ልታሻሽሉት ሃሳብ ገባችሁ? እስኪ መልሱልኝ ቃል ስጋ ስለመሆኑ ምስጢር ነውን ? ከብርሃን የተገኘ ብርሃን ፣ ከእውነተኛ አምላክ የተገኝ እውነተኛ አምላክ ፣ የተወለደ እንጂ የተፈጠረ ያይደለ ፣ በባህርይው ከአብ ጋር የሚስተካከል ፣ ሁሉ በእርሱ የሆነ የሚለውን ህፀፅ አገኛችሁበት? ወይንስ ከሁሉ በላይ በምትሆን ሃዋርያት በሰሯት በአንዲት ቤተ-ክርስቲያን እናምናለን የሚለው ጎረበጣችሁ? አለዚያስ ሃጢአት በሚሰረይባት በአንዲት ጥምቀት እናምናለን የሚለውን የክርስቶስ ትእዛዝ አይደለም ትላላችሁ? ስለ ክቡር መስቀሉ ሃይል የተነገረውንስ ልትክዱስ ትዳዳላችሁ? ወይንስ የዘላለም መጥፊያ የሚሆናችሁን የእመቤታችን ዘላለማዊ ድንግልና፣ አማላጅነትና የአምላክ እናትነት አለማመንን ገንዘብ አደረጋችሁ? አለዚያስ ፃድቃን ቅዱሳንን ንቃችሁ ራሳችሁን ፃድቃን አደረጋችሁ? እንዲህስ ከሆነ እንግዳ የሆነውን ትምህርታችሁን ከወዴት አመጣችሁት? እስኪ መልሱልኝ መሬት ወድቃችሁ አመድ ነስንሳችሁ ፆምን ፆማችሁን? ይህንስ እንዳልል አላማውን በዘነጋው አገልግሎታችሁ ብዛት በመድከማችሁ ፆምን መፆም ትታችኅል፡፡ ፆምስ ካልሆነ ታዲያ ሱባኤ ገብታችሁ ሌቱን በትጋት በፀሎት በመቆም ፣ ቀኑን ሙሉ ቅዱሳን መፃህፍትን በመመልከት ተጠመዳችሁን? ይህንንም እንዳልል ውሏችሁ ፣ አዳራችሁና ተግባራችሁ በአለም ከተቆራኝነው ከእኛ ጋር ነው፡፡ ታዲያ ኦርቶዶክሳዊ መንፈሳዊነት በተለየው አንደበታችሁ መንፈስ ቅዱስ ፀጋውን አበዛልን ፣ ኢየሱስ ገለጠልን ትሉ ይሆንን? ነገር ግን የእግዚአብሄር ፀጋ ለዚያውም አዲስ ጥበብ ያለ ፆም ያለ ፀሎት እንዳይገኝ እናውቃለን፡፡ ታዲያ እናንተ የሃይማኖት መሰረትን ትቀይሩ ዘንድ የተነሳችሁ ከ318ቱ የኒቂያ ጉባኤ ሊቃውንት ትበልጡ ዘንድ ከእነ ቅዱስ ቄርሎስ የተሻለ ሃይማኖታዊ ግብር ታየባችሁን? እነዚያ የተወደዱ ሊቃውንት ግን “ ከአባቶች ከሃዋርያት ስትያያዝ የመጣች ከዚህ አትለፍ ፣ ከዚህ አትትረፍ ብለው የወሰኑዋት ፤ ሰውን ሁሉ ከአራት መአዘን የሰበሰበች ሃይማኖትን” አፅንተው፤ ከተመሰረተው መሰረት ሌላ መሰረት እንዳይመሰረት አዘዙ፡፡

እናንተ ተዋህዶን ልታድሱ የተነሳችሁ ፦ የተዋህዶ ቤተ-ክርስቲያን ስርአቷ አሪታዊ የሃዲስ ኪዳንም የፍቅር ብርሃን ያልበራባት መሰላችሁ ይሆን? ወይንስ ስርአቷ ክርስቲያናዊ እንዳልሆነ ሃሳብ ገባችሁ? እንደዚያ ካሰባችሁ የወንጌሉ ብርሃን ቤተ-ክርስቲያን ላይ በሙላት እንዴት እንደበራ የቤተ-ክርስቲያንን ስርአት ከየትኛው ጀምሬ ልናገር? መሰረቷም ጉልላቷም ክርስቶስ እንደሆነ አምና ስለምትሰራው ህንፃ ቤተ-ክርስቲያን ልናገር? ወይንስ ስለ የትኛው ልናገር? ስለ ሰጎኑ እንቁላል? ከሰገነቱ በታች ስላለው መሶበ-ወርቅ? በክርስቶስ ልደት ወቅት ሄሮድስ ያስጨፈጨፋቸውን ሰማእት ህፃናትን ጩኅት ስለሚያዘክረው በጣርያው ዙሪያ ስላሉት ትናንሽ ቃጭሎች ባወራ ይሻል ይሆን? ስለ በሩና ስለ መስኮቱ ? ስለ ቤተልሄም? ስለ ቅድስተ ቅዱሳን? ወይንስ ስጋወ ደሙ ስለሚከብርበት ታቦቱ ልናገርን? እንዲህ ስርአቷ በሙሉ ባለሙያ ሴት በጥንቃቄ እንዳሰናዳችው ማእድ በአግባቡ ተሰናድቶ አንዱ ካንዱ ጋር ሳይጋጭ ፣ አንዱ አንዱን ሳያጠፋው ፤ ከመሰረቷ እስከ ጉልላቷ በወንጌል ባሽበረቀችው ቤተ-ክርስቲያን ላይ ክርስቶስንና የክርስቶስን መለኮታዊ ፈቃድ የሚቃወም ምን ነገር አገኛችሁና እናድስ ብላችሁ ተነሳችሁ? ይህስ የቤተ-ክርስቲያን ውበት ምእመናን እንደ ቤተ-ክርስቲያናቸው ስጋቸው ነፍሳቸውና ልቦናቸው እንዲሁ በወንጌል እያሽበረቀ ለአለም ሁሉ ክርስቶስን በህይወት እንዲሰብኩ የሚያነሳሳ መሆኑን ልብ አላላችሁም? ወይንስ እናንተ ዲያቢሎስን ያስከፋውን ይህን እፁብ ድንቅ የቤተ-ክርስቲያን ጌጥ ታፈርሱ ዘንድ ሰልፋችሁን ከሚጠፉት ጋር አደረጋችሁ? እንዲህስ ካልሆነ የትኛውን ታድሱ ዘንድ ፈለጋችሁ? በቅዱሳን ስም በየወሩ የሚዘከረውን ዝክር ከወንጌል ውጭ ነው ትላላችሁን? ምእመናንስ የሰንበቴውን በረከት ሊካፈሉ ሲሰባሰቡ ስትመለከቱ ትናደዳላችሁ? ወይንስ በክርስቲያኖች ቤት ዘወትር በልደታ የሚቀቀለውን ንፍሮ ትርጉሙ ቢጠፋባችሁ መሳለቅ ወደዳችሁን? እናንተ ለፀሎት ለፆምና ለምስጋና መንፈሳዊነታችሁ ቢደክም ፣ አለማዊ ደስታና ጥጋብ በእናንተ ላይ ቢሰለጥን ፣ የስጋዊ ሃብት ምቾት ከተጋድሎ ቢያስቀራችሁ ፤ ቅዳሴ ያጥር ዘንድ እንደ አዋቂ ትማከራላችሁን? ወይንስ ከ7ቱ አፅዋማት እየመረጣችሁ ይህንን ፁሙ ፣ ይህ እንኳን አይጠቅምም ለማለት እንዴት ትደፍራላችሁ?

እናንተ ተዋህዶን ልታድሱ የተነሳችሁ ፦የሆነ ሆኖ ከቀደሙት ቅዱሳን አባቶቻችን አብልጠን እናንተን እንሰማ ዘንድ የተገባ ይመስላችኅል? ቅዱስ ያሬድ ያከበራትን ፣ የኖረባትን ፣ ያፀናትን እምነት ትተን አላፊ ጠፊ በሆነው በዚህ አለም ወሬያችሁ ተታለን የምንወጣ እንደሆን ታስባላችሁ? ወይንስ አባታችን አቡነ ትክለሃይማኖት ህይወታቸውን በሙሉ በስርአቷ የተመላለሱባትን ፣ ቅዳሴዋን አስቀድሰው የቀደሱባትን ፣ የእጣኑን ሽታ አሽትተው እጣን ያጠኑባትን ፣ ጥምቀቷን ተጠምቀው ያጠመቁባትን ፣ ትምህርቷን ተምረው ያስተማሩባትን ፣ ከአለማዊ ግብር ተለይተው እንደ ተዋህዶ ስርአት በገዳም ራሳቸውን ወስነው በፆም በፀሎትና በተጋድሎ ከክርስቶስ ጋር የተገናኙባትን መሰላል ትተን በገንዘብ ፍቅር የወደቃችሁትን ፣ በአለም ወዳሴ ያበዳችሁትን ፣ ከፆም ከፀሎት የተለያችሁትን እናንተን እንሰማ ዘንድ የምንፋጠን ሞኞች መሰልናችሁን? እናንተስ በየትኛው መልካም መንፈሳዊ ፍሬያችሁ ከአባቶቻችን ጋር ትደመሩ ዘንድ አዲስንም ትምህርት ታመጡ ዘንድ ቻላችሁ? ከመጀመሪያወቹ የክርስትና መናንያን ቀዳሚ የሆኑት የተወደዱት አባ ጳውሊ ፦ ከ90 አመታት በላይ አንድን ሰው እንኳን ሳያዩ በፆም በፀሎት ተወስነው በሚኖሩ ጊዜ ፤ አባታችን አባ እንጦንስ በእግዚአብሄር ተመርተው አባ ጳውሊን ሊጎበኙ ቢመጡ ምስጉን የሆኑ አባ ጳውሊ አባ እንጦንስን አንድን ነገር እንዲያመጡላቸው ግድ አሏቸው ፤ ይሔውም አቡነ አትናቴዮስ የኦርቶዶክስ እምነትን በ318ቱ ሊቃውንት ህግ ካፀና በኅላ ለመነኮሳት ልብስ የሚሆን ስለአዘጋጀ ከዚህ የመነኮሳት ልብስ አንድ እንዲያመጡላቸው ነበር ፤ ይህንም የሚያደርጉት አትናትዮስ ያፀናትን የኦርቶዶክስ እምነትን ህይወታቸውን ሙሉ እንደያዙ መኖራቸውን ህዝቡ ሁሉ እንዲያውቅ ለምስክርነትም እንዲሆን ተናገሩ፡፡ ታዲያ እናንተ ኦርቶዶክስን ታድሱና ትቀይሩ ዘንድ የተነሳችሁ ከእነኘህ ፅኑ ፣ ቅዱስ ፣ ክርስቶስን የመሰሉ የምድር መላእክት ከሆኑ ስለ ወንጌልም ሁሉን ትተው ክርስቶስን ከተከተሉት አባቶች ትበልጡ ዘንድ ተገባችሁን? እንግዲህስ እወቁት እኛስ እናንተ በምትነግሩን ነፍስንም ደስ የማያሰኝ አዲስ እውቀት በመንግስተ ሰማያት ከምንኖር ይልቅ እነ አባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ ፣ እነ ቅዱስ ያሬድ ፣ እነ ቅዱስ ዮሃንስ አፈወርቅ ፣ እነ ቅዱስ ጊዮርጊስ ፣ እነ አቡነ ተክለሃይማኖት የነገሩንን ይዘን ፣ የኖሩበትን ህይወት ኖረን ሲኦል እንድንገባ እንመርጣለን፡፡ ነገር ግን መንግስተ ሰማያት ለእንደዚህ ያሉ ቅዱሳን አባቶች የተዘጋጀች እንደሆነች የክርስቶስ ወንጌል ይመሰክራል ፤ ይህችም ቅድስት ቦታ አለምን ንቀው ፣ ርቀው ፣ ጠልተው በእግዚአብሄር ትእዛዝ ለሚፀኑት እንደተሰጠች ፣ የመንፈስ ቅዱስ ፀጋም በፀሎት ፣ በፆም ፣ ትሩፋትን አብዝቶ በመስራትና በመሳሰሉት መንፈሳዊ ተግባራት የሚገኝ እንደሆነ እናውቃለን፡፡

እኛም ክብር የሚገባው ኢየሱስ ክርስቶስ የበግ ለምድ ለብሰው ከሚመጡ በውስጣቸው ግን ነጣቂወች ተኩላወች ከሆኑ ተጠበቁ ፤ እንዚህንም ከፍሬያቸው ትለዩዋቸዋላችሁ እንዳለን ፤ ወንጌል በሚያበራልን ብርሃን ተኩላወችን ነቅሰን እናወጣ ዘንድ ይገባናል፡፡ እናንተም ተዋህዶን ታድሱ ዘንድ የተነሳችሁ ለሰው ሁሉ የሚታየው ፍሬያችሁ መልካም አይደለምና አስቀድማችሁ ራሳችሁን በንስሃ ታድሱ ዘንድ አይሻላችሁምን? ስለ ገንዘብም ያላችሁን መገዛትና መመካት ትተው ዘንድ የተገባ ነው፡፡እናንተ ግን መንፈሳዊ ሰው የመንፈስን ስራ በገንዘብ እንዳይለውጥ አባቶቻችን ሃዋርያት መንፈስ ቅዱስን የማሳደር ፀጋን በፈቀደው ሰው ላይ ለማውረድ እንዲችል ከሃዋርያት ጋር ፀጋውን በገንዘብ ሊደራደር የሞከረውን ከንቱ ሰው የዘለፉበትን ነገር እረሳችሁት፡፡”የሚያበራየውን በሬ አፉን አትሰሩት” የሚለውን የአምላክ ትእዛዝ እንደገዛ ፈቃዳችሁ ለሆዳችሁ እንዲስማማ አድርጋችሁ ተረጎማችሁት፡፡የክርስቶስን ወንጌልና የመንፈሳዊውን ስራ በገንዘብ የመሽጣችሁን ነገር “ለሰራተኛ ደመወዙ ይገባዋል” በሚለው እድሜያችሁን ሙሉ የማትጨርሱትን ምድራዊ ሃብትን ማከማቻ አደረጋችሁት፡፡ የኦርቶዶክስ መንፈሳዊ አባቶቻችን ግን እጅግ ውድ የሆነውን መንፈሳዊውን ፀጋ እጅግ ርካሽ ለሆነው አለማዊ ንዋይ እንዳይለውጡትና ከንቱ በሆነው ግብር እንዳይተባበሩ ከህሊናቸውና ከዚህ አለም አምሮት ጋር እድሜያቸውን ሙሉ ታገሉ ፤ ስላሽነፉትም ለክርስቲያን ወገኖች ሁሉ ትምክህትና አርአያ ተባሉ፡፡እናንተ ግን ከዚህ አለም ናችሁና የአለም ምኞቷና አምሮቷ ጠልፎ ጣላችሁ፡፡ መንፈሳዊ ከመባልም የለየለት አለማዊ ነጋዴ ወጣችሁ፡፡ ስለነጋዴነታችሁም መንፈሳዊውን ስብከትም ሆነ መዝሙር ስታዘጋጁ የመንፈሳዊው ጌታ እግዚአብሄር ምን ብናገር ይወዳል(what God want or what the people need) ከማለት ይልቅ የዚህ ስብከትና መዝሙር ገዥ ምን ባዘጋጅለት ብሩን ደስ ብሎት ያወጣል ( what the people want) በሚል ለወጣችሁ፡፡በዚህም እግዚአብሄርን ማገልገል ትታችሁ ስለ ገንዘብ ጥማት የሰይጣንና የሰው ባርያ ሆናችሁ፡፡ በአለማዊውም ምቾትና መንደላቀቅ በሚገኝ በሚስረቀረቅና በሚያስገመግም ድምፅ ፣ ስለ ሃጢአት ሰውን ከመገሰፅ ይልቅ ፃድቅ በማድረግ ፣ በትህትና ራስን ዝቅ ከማድረግ ፈንታ በትእቢት ከሁሉ በላይ ራስን መስበክና ማስወደድን በማብዛት መልካም የነበረውን ሰው አለማዊ በሆነው ተግባራችሁ ከመንፈሳዊ ስነምግባር ይወጣ ዘንድ ታፋጥኑታላችሁ፡፡እንግዲህ እኔ ደግሞ የእናንተን ሃጢአት ስዘረዝር ራሴን ፃድቅ ማድረጌ ነውን?አይደለም ፤ የእናቴን ቤት አጥር ልታፈርሱ ስትነቀንቁ ስላየኅችሁ እንጂ ፡፡ታዲያ እስኪ ንገሩን ፦ የትኛው መልካም ስራችሁ ተዋህዶን ልታድሷት አደረሳችሁ?

ለመሆኑ ተዋህዶን ታድሷት ዘንድ የተነሳችሁ እናንተ እነማን ናችሁ? የክርስቶስን ወንጌል ለመስበክ ቤተ-ክርስቲያን ከምትችለው በላይ ለዚያውም የታወቀ አለማዊ መምህር ከሚጠይቀው ገንዘብ የሚበልጥ ካልተከፈለን ወንጌልን አንሰብክም የምትሉ ብኩኖች ፤ እኛም ካልሰበክን ጉባኤው ይፈታል የምትሉ ትእቢተኞች ስትሆኑ ፦ ከአለም ኑሮ ፣ መንፈሳዊ ኑሮ እንዲበልጥ ፤ ከገንዘብ ፍቅር የእግዚአብሄር ፍቅር እንዲሻል እንዴት መናገር ትችላላችሁ? ወይንስ በተገኘው አጋጣሚ ሁሉ ባከማቻችሁት የደሃ ገንዘብ ፤ እናንተ እያማረባችሁ ፣ እየወዛችሁ ፣ እየወፈራችሁ ና ትካሻችሁ እያበጠ ስትታዩ የምትሰብኩት ምእመናን ደግሞ እየጎሰቆሉ ፣ እየገረጡና እየከሱ መምጣታቸው መልካም እረኛ የሚያደርጋችሁ ይመስላችኅል? የተዋህዶ እውነተኛ እረኞች ግን ክርስቶስ እንዳደረገ በጎቹ እንዳይባዝኑበት ራሱን መስዋእት ያደርጋል፡፡ ዛሬ ዛሬ የተዋህዶ እውነተኛ እረኞች ከአንዱ ሃገር ወደ ሌላው ፣ ካንዱ መምህር ወደ እዚያኛው እየተንከራተቱ የክርስቶስን ወንጌል አምልተው ፣ አመስጥረው ቅኔን ፣ ዜማን ፣ ትርጓሜን ፣ አቋቋምን እድሜ ልክ ተምረው ሊቀ ሊቃውንት ቢባሉ ፦ ተራራ ለተራራ ፣ ዋሻ ለዋሻ ፣ ገጠር ለገጠር እየዞሩ ገዳማቱ እንዳይፈቱ ፣ የአብነት ትምህርት ቤቶች እንዳይበተኑ ፣ ምእመናን ከምግባር ከሃይማኖት እንዳይርቁ በ 40 ና በ 80 ብር ቤተ-ክርስቲያናቸውን ደከመኝ ሰለቸኝ ሳይሉ ሲያገለግሉ ፤ እናንተ ግን ምን ፣ መቼና የት እንደተማራችሁ እንኳን በቅጡ የማይታወቅ በሚልዮን የሚቆጠር ገንዘብን በቤተ - ክርስቲያን ስም ስታስገቡ ከእግዚአብሄር ይልቅ ለገንዘብ መገዛታችሁ እንደሆነ አታውቁምን? ወይንስ የገንዘብ ፍቅር መልካም ስራን ሁሉ እንደሚያጠፋ አልተማራችሁም? ወይንስ ደመወዛችሁ ይብቃችሁ የተባሉትን እውነተኛ የተዋህዶ ሊቃውንት የክርስቶስን ወንጌል በገንዘብ እንዲቀይሩ ፈተና እንደሆናችሁባቸው አልተረዳችሁምን?

ፕሮቴስታንታዊ በሆነው ስብከታችሁና መዝሙራችሁ ደግሞ የቅዱሳንን በትህትና ዝቅ ማድረግ እንደ ውርደት ቆጥራችሁ ራሳችሁን በሰውና በአምላክ ፊት ከፍ ከፍ ስታደርጉና ራሳችሁን ስታፀድቁ ፤ ተዋህዶ ግን ስለቅዱሳን መናገር አንድም ህይወታቸው ትምህርት ስለሆነ አንድም በረከታቸውን ለመካፈል እንደሚረዳ ስታስተምር ፣ እናንተ ግን የቀደሙ ቅዱሳን አባቶችን ማስረሳትን አንድም ምእመናንን ከበረታቸው ለማስወጣት አንድም በቀደሙት አባቶች መልካም ተጋድሎ የእናንተ ስራ እንዳይጋለጥ ስራየ ብላችሁ ተያያዛችሁት፡፡እናንተ ሌባ ሌባነቱ ቢታወቅ ፈቃዱን ይፈፅም ዘንድ ስለማይችል ፣ አመቺ ጊዜ እስኪያገኝ መልካም ሰው መስሎ ለመታየት ጥረት እንደሚያደርግ ፤ እናንተም አላማችሁን ሳታሳኩ ተሃድሶነታችሁ እንዳይጋለጥ በመዝሙራችሁና በስብከታችሁ ውስጥ በጥቂቱ ስለ አምላክ እናት ከመናገር ያለፈ እስኪ ስለ ሰማእቱ ጊዮርጊስ ፣ ሰማእቱ እስጢፋኖስ ፣ አቡነ ዘርአ ብሩክ ፣ አቡነ አረጋዊ ፣ አቡነ ሃብተ ማርያም ፣ ቅድስት አርሴማ ፣ ቅድስት ክርስቶስ ሰምራ፣ስለ ቅዱሳን መላእክት ፣ ስለ ሌሎችም ቅዱሳን ሁሉ በስህተት እንኳን የት ቦታ አስተማራችሁ? ነገር ግን ተዋህዶ እግዚአብሄር በቅዱሳኑ ድንቅ ነው የሚለውን ታምናለች ታስተምራለችም፡፡ ይህንንም የየወሩን እለታት በስማቸው ለመታሰቢያቸው ሰጥታ ትዘክራቸዋለች፡፡ እናንተ ግን ልጆቿ አይደላችሁምና ከእርሷ ያልሆነ አዲስን ዘር ትዘራላችሁ፡፡ እስኪ ንገሩን ፦ ቅዱስ ጳውሎስ እኔ ክርስቶስን እንደመሰልኩ እኔን ምሰሉ እንዳለ እነዚህን ቅዱሳን እንደታዘዝን የኑሯቸውን ፍሬ እያየን በእምነት እንመስላቸው ዘንድ ካልቻልን መንፈሳዊነትን ከማን እንማር ዘንድ ትወድዳላችሁ? ከእናንተ እንማር ዘንድ ፈቃድ ካላችሁስ ህይወታችሁን አይተን እንማርበት ዘንድ መልካሙ ፍሬያችሁ የት አለ? ወይንስ እውር እውርን ይመራው ዘንድ ይችላልን? እንደዚያስ ከሆነ መንፈሳዊ አይን በተለየው ህይወታችሁ የተዋህዶን ህፀፅ እንዴት ልትመለከቱ ቻላችሁ? ወይንስ ስለ ፆም ስለ ፀሎት መስማታችንን ትተን የእናንተ ችሎታ ስለሆነው በክርስቶስ ወንጌል እንዴት ገንዘብ መስራት ይቻላል? የሚለውን እናጥና ይሆን? ወይንስ ራስን በማክበድና በማስወደድ እንዴት የሰውን ከበሬታ ማገኘት እንደሚቻል እንማር? እኛስ ይህንን የሰይጣን ስራ እንዳንሰራ ፣ ሲጀመርም እናንተን እንዳንሰማ ፣ ከተኩላወችም ጋር እንዳንተባበር ክርስቶስ አስቀድሞ አዘዘን፡፡

ፕሮቴስታንታዊ በሆነው ስብከታችሁና መዝሙራችሁ ነፍስ የተለየው ስጋ ምውት እንደሆነ ከስራም የተለየ እምነት ባዶ ነው የሚለውን የተዋህዶ አስተምሮ ትታችሁ ለአለማዊ አኗኗር የሚስማማውን ስራ ስለተለየው እምነት አብዝታችሁ ታስተምሩ ዘንድ ደከማችሁ፡፡ነገር ግን ተዋህዶ ወርቅ ወርቅነቱ በእሳት ተፈትኖ እንዲታወቅ እምነትም ከዚህ አብልጦ በስራ እንዲፈተን ለልጆቿ ታስተምራለች፡፡ይህን የሚያውቁ ልጆቿም ዘወትር ለትሩፋት ይፋጠናሉ፡፡ነገር ግን እናንተ ፍሬ የማያፈራ ፣ ክብር የሚገባው አብም ያልተከለው የሚነቀል ዘርን በአሽዋ ላይ ትዘሩ ዘንድ ሮጣችሁ፡፡ፕሮቴስታንታዊ በሆነው እምነታችሁ በገዳም ተወስኖ እድሜን መጨረስ የሰነፎች ስራ ነው በማለት የአባ እንጦንስንና የአባ መቃርስን ትምህርት ሻራችሁ፡፡ነገር ግን በሰው ተከቦ ለአለም ሁሉ ወንጌልን ከመስበክ ፣ ተአምራትንም እያደረጉ ዋጋን ከሰው ከመቀበል ፤ ራስን ስለ ክርስቶስ ከሰው ለይቶ ፣ ከምቾት ርቆ ፣ ስጋን ለነፍስ አስገዝቶ ፣ አብዝቶ በመፆም ፣ አብዝቶ በመፀለይ ፣ የሌሊቱን ድምፀ አራዊት ታግሶ ፣ የሰይጣንን ድብቅና ግልፅ ፈተና ታግሎ ድል ማድረግ ምን ያክል አድካሚና ዋጋውም የቱን ያክል የበዛ እንደሆነ ዘነጋችሁ፡፡ እናንተ ግን ለስጋችሁ አምሮት ከዚህ ግርግር ከበዛበት አለም የተሻለ አታገኙምና ለገዛ ምቾታችሁ የእግዚአብሄርን ፈቃድ ትቃወማላችሁ፡፡ ታዲያ እስኪ ንገሩን ፦ በሁሉ ስህተት ሆናችሁ እያየን እናንተን እንሰማ ዘንድ የሚገባ ይመስላችኅል?

እንግዲህ የተወደደው አባት አባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ ኖሮበት ያለፈውን የቤተ-ክርስቲያናችን ዶግማና ቀኖና ይታደስ ዘንድ የምትሮጡ እናንተ እነማን ናችሁ? ወይንስ ማደስ (renew) የሚለውን ቃል መቀየር (change) ወይም ማሻሻል (upgrade) አድርጋችሁ ወሰዳችሁን? ማደስ ማለት ወደ ድሮው ወይም ወደቀደመው ነገር መመለስ (back to the Origional) እንደሆነ አላስተዋላችሁምን? ኦርቶዶክስን እናድሳት ስትሉስ ወደቀደመው ስርአቷ እንመልሳት ማለት እንደሆነ ካወቃችሁ ከቀደሙት ቅዱሳን አባቶች የተሻለ የቀደመችውን ሃይማኖት ታውቁ ዘንድ እንዴት ቻላችሁ? ነገር ግን የሰይጣን ምክር እንዳይዘነጋ የእናንተም ሃሳብ መልካም ስራን መስራት ሳይሆን አውሮፓውያንና አሜሪካውያን የራሳቸውን ህዝብ ከሃይማኖተኛነት አውጥተው አለማዊ አድርገውት ሲያበቁ ፦አሁን ደግሞ በሃይማኖት የፀኑትን የኦርቶዶክስ አማኝ ክርስቲያኖች ወደ አለማዊነት ወደሚያንደረድረው የፕሮቴስታንታዊ ምንፍቅና ማሰደድ ነው፡፡ ነገር ግን ቤተ-ክርስቲያን በክርስቶስ አለትነት ላይ የተመሰረተች ናትና የገሃነም ደጆች እንኳን አይችሏትም፡፡ እኛም ከቀደሙት ቅዱሳን አባቶች ይልቅ እናንተን ፤ ከመልካሙ መንፈሳዊ የህይወት ፍሬ ይልቅ የከረፋውን አለማዊ ህይወታችሁን አይተን እንታለል ዘንድ እንዳንችል እናንተ የናቃችኅቸው የቅዱሳን ፀሎት ዘወትር ይጠብቀናል ፡፡

እንግዲህ ምን እንላለን ፦ እንዚያ አምነው የነበሩ የካዱትንም ትመልሷቸው ዘንድ አትድከሙ የሚለውን የተወደደ የሃዋርያ መልእክት እንሰማ ዘንድ ይገባናል፡፡ እናንተ ግን መልካችሁን እንደ ዲያቢሎስ እየቀያየራችሁ መኖሩ ልብንና ኩላሊትን በሚመረምር በእግዚአብሄር ዘንድ የተጠላ መሆኑን አስተውሉና ለነፍሳችሁ እዘኑላት፡፡ እኛ ልክ ነን ካላችሁ ግን ውጡ ፤ እምነታችሁን ይዛችሁ እምነታችንን ልቀቁልን፡፡ ስለ እምነታችሁም በአደባባይ ስበኩ ፣ አውሩ ፣ አስተምሩ ፤ ነገር ግን የተዋህዶ ቤተ-ክርስቲያን አውደ ምህረት የእናንተ አይደለምና ውረዱ ፡፡ እግዚአብሄርም በውሽት ፣ በማጭበርበርና በማስመሰል እንደማይከብር ፣ በዚህም ሰወች ወደእርሱ ይመጡለት ዘንድ እንደማይፈልግ እወቁ፡፡ እናንተም ከእኛ ወገን የሆናችሁ ባለማወቅም ፣ በስንፍናም ከእነዚህ ጋር የምትተባበሩ የተዋህዶ ልጆች ስለ እናታችን ስለ ቅድስተ ቅዱሳን ድንግል ማርያም ብላችሁ ከፀረ-ተዋህዶ የዲያቢሎስ ተላላኪወች ተለዩ፡፡እናንተ ግን ተዋህዶን ልታድሱ የተነሳችሁ ፦ ከቀደሙት ቅዱሳን አባቶቻችን አብልጠን እናንተን እንሰማ ዘንድ የተገባ ይመስላችኅል? ወይንስ ቅዱስ ያሬድ ያከበራትን ፣ የኖረባትን ፣ ያፀናትን እምነት ትተን አላፊ ጠፊ በሆነው በዚህ አለም ወሬያችሁ ተታለን የምንወጣ እንደሆን ታስባላችሁ?

ወስብሃት ለእግዚአብሄር ፣ ወ ለወላዲቱ ድንግል ፣ ወ ለመስቀሉ ክቡር፡፡