Monday, 27 June 2011
ተዓምርህን አየን
Thursday, 23 June 2011
እግዚአብሔር የቅዱሳንን አማላጅነት እንድንጠቀም ጠይቆናል !
Wednesday, 22 June 2011
የቅዱሳን አማላጅነት - ስለኛ መጸለይ ነው! እግዚአብሔር የቅዱሳንን አማላጅነት እንድንጠቀም ጠይቆናል !
Tuesday, 21 June 2011
የጥፋት ሃይማኖት
Saturday, 11 June 2011
ድንጋይ ስድብ ነው ወይ
Friday, 3 June 2011
ሊነበብ የሚገባ ጽሁፍ,, ተዋህዶን ታድሷት ዘንድ የተዘጋጃችሁ እናንት እንማን ናችሁ ?

ክብር የሚገባህ አምላካችን እግዚአብሄር ሆይ ፦ የአለማት ሁሉ አስገኝ ፣ የፍጥረታት ሁሉ ጌታ ፤ እኔ ልጅህ እንዳልል የአባትነት ክብርን ያልሰጠሁህ ፣ እኔ ባሪያህ እንዳልል የጌትነት ትእዛዝህን ያልፈፀምኩ ለምንም የማልጠቅም የወደቅሁ ሰው ስሆን አሁን ግን እንደ አዋቂ ፣ ጥበብን ገንዘብ እንዳደረገ በደምህ ስለዋጃሃት ቤተ-ክርስቲያን በድፍረት እናገር ዘንድ ራሴን አዘጋጅቻለሁና ማስተዋሉ አቅቶኝ ፍቅሩ ጎድሎኝ አንተን የሚያሳዝን ቃላትንና ሃረጋትን ብጠቀም ስለ ተወዳጇ እናትህ ስለ ቅድስት ድንግል ማርያም ብለህ ይቅርታህን እንድትሰጠኝ እለምንሃለሁ፡፡ አምላክ ሆይ አንተ በእውነት ምስጋና ይገባሃል፡፡
ይህን ፅሁፍ ሳዘጋጅ አሁን ካየሁበት አተያይ አልፌ ከተለያዩ አቅጣጫወች ማየት የሚገቡኝ ፣ ነገር ግን ከእኔ የተሻሉ ሰወች እንዲያዩት በማለት ያለፍኳቸው ጉዳዮች ቢኖሩም ይህን ፅሁፍ ግን ሊያሳጥረው አልቻለም፡፡የሆነው ሆኖ አሁን ያየሁበት አተያይም ቢሆን ሊፅፉት የሚገቡት በቤተ-ክርስቲያናችን ያሉ ሊቃውንት ይሆኑ ዘንድ እንዲገባም አምናለሁ፡፡ደግሞም የክርስቶስን በጎች ይጠብቁ ዘንድ ክርስቶስ አደራ ያላቸው የቤተ-ክርስቲያን እረኞች በክርስቶስ ጥበብ እየተመላለሱ ህዝቡን ሁሉ በመልካም ማሰማሪያ የሚያሰማሩቱ ፦ ስለ ወቅቱ እንቅስቃሴና መዘዝ የሚገባውን እርምጃ እየወሰዱ እንደሆነ እንኳን ባምንም ፣ ከእረኞች ወገን ያልሆንኩት እኔ ፣ ለዚያውም ገራም ካልሆኑት አስቸጋሪ በጎች መካከል የምመደብ ፣ በዚህ ተግባሬ የእውነተኞቹን እረኞች ስራ እቃወም የሆንን እያልኩ እፈራለሁ፡፡የሆነ ሆኖ ቤተ-ክርስቲያን ማለት እናት ማለት ስለሆነ እኔም እንደ ቤተ-ክርስቲያን ልጅነቴ መከራዋንና ፈተናዋን ዝም ብየ አይ ዘንድ የሚገባ ስላልሆነ ይህን ፅፍኩ፡፡
ቤተ-ክርስቲያን ተሃድሶ ያስፈልጋታል የሚሉትን አዳሾች ከመሞገቴ አስቀድሞ ተሃድሶ የለም ፣ ሰነፎች የፈጠሩት የሃሰት ወሬ ነው የሚሉትን ጥያቄ ልጠይቃቸው፡፡ እናንተ ተሃድሶ የለም የምትሉ ወንድሞቼና እህቶቼ በተለይም በ40 ና በ80 ቀን በስላሴ ስም የተጠመቃችሁ ፣ እናንተ በክርስቶስ የባህርይ አምላክነት የምታምኑ ፣ የድንግል ማርያም ፍቅር በልቦናችሁ የሚቃጠል ፣ የቅዱሳን የሰማእታት ወዳጆች ፣ የተዋህዶ ቤተ-ክርስቲያናችሁ ህግና ስርአት ውበት ጌጣችሁ የሆነላችሁ፤ እስኪ መልሱልኝ ፦የዲያቢሎስን የጥፋት አሰራር የክፋቱንም ጥበብ እረሳችሁት? የቀደመውስ እባብ የመጨረሻው ቀን እንደደረሰ አውቆ ዝናሩን በቤተ-ክርስቲያን ላይ እያርከፈከፈ እንደሆነ አላስተዋላችሁም? ወይንስ ዲያቢሎስ መልካም የሆነውን መንፈሳዊ እሴት ይሰርቅ ዘንድ የሚተጋ ሌባ እንደሆነ ዘነጋችሁ? አለዚያስ ተዋህዶ ቤተ-ክርስቲያናችሁ የመንፈሳዊ ፀጋ ባለሃብት እንደሆነች አታምኑም? ክርስቲያኖች፦ ተዋህዶ ቤተ-ክርስቲያናችሁ በዚህ ጊዜ ያለች ብቸኛ በእግዚአብሄር ደም የተዋጀች ፣ መሰረቷና ጉልላቷ ክርስቶስ የሆነላት ፣ ዘወትርም በቅዱሳን ፀሎት የምትጠበቅ ፣ ዶግማና ቀኖናዋም ሰማያዊ እንደሆነ ካመናችሁ ዲያቢሎስ ይህን ሁሉ እየተመለከተ ዝም የሚል ይመስላችኅል? የዲያቢሎስስ ተግባር መልካሙን ሁሉ ለክፋት ማስገዛት እንደሆነ ትዘነጋላችሁ? እንግዲህስ ዲያቢሎስ ሌባ እንደሆነ ሌባም ሊሰርቅ ወርቅና ብር ካለበት ከሃብታም ግቢ ይገባ ዘንድ ይፋጠናል እንጂ የደሃ ቤትን እንዳይሰረስር ቤተ-ክርስቲያንም በአለም ያለች የሰማያዊ ፀጋ ባለሃብት እንደሆነች ካወቅን ወርቅና ብር ተከማችቶ የሚቀመጥበትን ነቅቶ ከሌባ እንደማይጠብቅ ሰነፍ ሰራተኛ እንሆን ዘንድ የተገባ ነውን? እንግዲህ አንዘነጋ ፣ የዲያቢሎስ ፈተናወችና መከራወች በየወቅቱ ልዩ ልዩ መሆናቸውን ተገንዝበው ፤ በአለም ሳላችሁ መከራ አለባችሁ የተባለው አማናዊ ቃል ይፈፀም ዘንድ የእግዚአብሄር የሆኑቱ ዘወትር በመከራ ይፈተናሉ፡፡ ያለ መከራም አክሊል ይገኝ ዘንድ አይቻልምና ፈተናውን ሁሉ በጥበብና በትእግስት የሚያሳልፉቱ ቅዱሳን ደግሞ በመከራቸው እንዲመኩ እናውቃለን፡፡ ታዲያ እንደዚህ ከሆነ የተሃድሶን ነገር እንደምን አላወቃችሁም? በህንድ ፣ በአርመን ፣ በሶሪያ ፣ በግብፅ ና በኤርትራ የተደረገውን አልተማራችሁም? ወይንስ አለማወቅን እውቀት አድርጋችሁ ተቀምጣችኅል? ወይንስ ተሃድሶ የሚለውን ስያሜ የፕሮቴስታንቶች ተንኮል በኦርቶዶክስ ቤተ-ክርስቲያን ላይ በሚለው ቢተካ ልባችሁ ይገኝ ይሆን? ወይንስ በተሃድሶ ሴራ ውስጥ ተባባሪ ሆናችሁን? እኔ ግን ርቃችሁ እንደሆነ እፈራለሁ ፦ የዚህ አለም ፍቅር ወይስ ጣጣ ከእግዚአብሄር እቅፍ አወጣችሁ? ከቤተ-ክርስቲያናችሁስ የእጣን ሽታ የአለም የክርፋቷ ጣእም በለጠባችሁ? እንግዲህ ተመለሱ ፤ ወደ እናታችሁ ጉያ ግቡና ታቀፉ ፤ ቤተ-ክርስቲያን እናታችሁ ናትና በደስታዋም በመከራዋም ከጎኗ አትለዩ ፤ በወቅት የማይገኝ የሩቅ ዘመድም አትሁኑ ፤ ቅረቧት ክበቧት ዘወትርም ፊቷን ተመልከቱ ፤ ያለቀሰች እንደሆነ አብራችሁ እያለቀሳችሁ እንባዋን ታብሱላታላችሁ ፤ አዝና ከሆነ ከጎኗ ሆናችሁ ሃዘኗን ትጋራላችሁ ፤ ብርድና ቁር ቢፈራረቁባት ፣ ረሃብና ጥማት ቢያደክማት ጉልበተኛ ቢበረታባት ደጀን አለኝታ ትሆኑላታላችሁ፡፡ እንዲህ ተብሎ እንደተፃፈ ፦ፅዮንን ክበቧት በዙሪያዋም ተመላለሱ፡፡ እንግዲህ በዚህ ዘመንም በቤተ-ክርስቲያን ላይ የደረሰው መከራ በረከሰው፣ በተወገዘውና በከረፋው የምንፍቅና አስተምሮ ታጅለው ጥንታዊቷን እምነት ሊያድሱ የተነሱ ደፋር ተሃድሶወች እንደሆኑ ልብ እንበል ፡፡ እነዚህ በቤተ-ክርስቲያን ቅጥር ያሉ ፣ በቤተ-ክርስቲያን ማእድ የሚመገቡ ፤ ነገር ግን ሆዳቸው አምላካቸው ፣ ሃሳባቸው ምድራዊ ፣ የዲያቢሎስ ባርያወች የሆኑ ተዋህዶን እናድስ ብለው በዲያቢሎስ ጥበብ ተነስተዋልና ሃገራችን በሰማይ የሆን እኛ የቀደሙ አባቶቻችንን ደጀን አድርገን በክርስቶስ ጥበብ እንረታቸው ዘንድ ይገባል፡፡ ስለዚህ እናንተ ወንድሞቼና እህቶቼ በትክክለኛይቱ ቤተ-ክርስቲያን ላይ መከራ እንደመጣ ፣ መምጣቱም ግድ እንደሆነ ካመናችሁ ፦ መከራው ምን እንደሆነ ቀርባችሁ ተማሩ ፤ ሰውንም ከማድነቅና ከማገልገል እግዚአብሄርን እናገለግል ዘንድ ለቤተ-ክርስቲያናችንም ዘብ እንቆም ዘንድ እንትጋ፡፡ እንዲህም እንድናደርግ አምላካችን እግዚአብሄር ይርዳን፡፡
እናንተ ግን ተዋህዶን ልታድሱ የተነሳችሁ አዳሾች ፦ ተዋህዶን ታድሱ ዘንድ ምን ህፀፅ ጉድለት አገኛችሁባት? የትኛውንስ የሃይማኖት ዶግማ ልታሻሽሉት ሃሳብ ገባችሁ? እስኪ መልሱልኝ ቃል ስጋ ስለመሆኑ ምስጢር ነውን ? ከብርሃን የተገኘ ብርሃን ፣ ከእውነተኛ አምላክ የተገኝ እውነተኛ አምላክ ፣ የተወለደ እንጂ የተፈጠረ ያይደለ ፣ በባህርይው ከአብ ጋር የሚስተካከል ፣ ሁሉ በእርሱ የሆነ የሚለውን ህፀፅ አገኛችሁበት? ወይንስ ከሁሉ በላይ በምትሆን ሃዋርያት በሰሯት በአንዲት ቤተ-ክርስቲያን እናምናለን የሚለው ጎረበጣችሁ? አለዚያስ ሃጢአት በሚሰረይባት በአንዲት ጥምቀት እናምናለን የሚለውን የክርስቶስ ትእዛዝ አይደለም ትላላችሁ? ስለ ክቡር መስቀሉ ሃይል የተነገረውንስ ልትክዱስ ትዳዳላችሁ? ወይንስ የዘላለም መጥፊያ የሚሆናችሁን የእመቤታችን ዘላለማዊ ድንግልና፣ አማላጅነትና የአምላክ እናትነት አለማመንን ገንዘብ አደረጋችሁ? አለዚያስ ፃድቃን ቅዱሳንን ንቃችሁ ራሳችሁን ፃድቃን አደረጋችሁ? እንዲህስ ከሆነ እንግዳ የሆነውን ትምህርታችሁን ከወዴት አመጣችሁት? እስኪ መልሱልኝ መሬት ወድቃችሁ አመድ ነስንሳችሁ ፆምን ፆማችሁን? ይህንስ እንዳልል አላማውን በዘነጋው አገልግሎታችሁ ብዛት በመድከማችሁ ፆምን መፆም ትታችኅል፡፡ ፆምስ ካልሆነ ታዲያ ሱባኤ ገብታችሁ ሌቱን በትጋት በፀሎት በመቆም ፣ ቀኑን ሙሉ ቅዱሳን መፃህፍትን በመመልከት ተጠመዳችሁን? ይህንንም እንዳልል ውሏችሁ ፣ አዳራችሁና ተግባራችሁ በአለም ከተቆራኝነው ከእኛ ጋር ነው፡፡ ታዲያ ኦርቶዶክሳዊ መንፈሳዊነት በተለየው አንደበታችሁ መንፈስ ቅዱስ ፀጋውን አበዛልን ፣ ኢየሱስ ገለጠልን ትሉ ይሆንን? ነገር ግን የእግዚአብሄር ፀጋ ለዚያውም አዲስ ጥበብ ያለ ፆም ያለ ፀሎት እንዳይገኝ እናውቃለን፡፡ ታዲያ እናንተ የሃይማኖት መሰረትን ትቀይሩ ዘንድ የተነሳችሁ ከ318ቱ የኒቂያ ጉባኤ ሊቃውንት ትበልጡ ዘንድ ከእነ ቅዱስ ቄርሎስ የተሻለ ሃይማኖታዊ ግብር ታየባችሁን? እነዚያ የተወደዱ ሊቃውንት ግን “ ከአባቶች ከሃዋርያት ስትያያዝ የመጣች ከዚህ አትለፍ ፣ ከዚህ አትትረፍ ብለው የወሰኑዋት ፤ ሰውን ሁሉ ከአራት መአዘን የሰበሰበች ሃይማኖትን” አፅንተው፤ ከተመሰረተው መሰረት ሌላ መሰረት እንዳይመሰረት አዘዙ፡፡
እናንተ ተዋህዶን ልታድሱ የተነሳችሁ ፦ የተዋህዶ ቤተ-ክርስቲያን ስርአቷ አሪታዊ የሃዲስ ኪዳንም የፍቅር ብርሃን ያልበራባት መሰላችሁ ይሆን? ወይንስ ስርአቷ ክርስቲያናዊ እንዳልሆነ ሃሳብ ገባችሁ? እንደዚያ ካሰባችሁ የወንጌሉ ብርሃን ቤተ-ክርስቲያን ላይ በሙላት እንዴት እንደበራ የቤተ-ክርስቲያንን ስርአት ከየትኛው ጀምሬ ልናገር? መሰረቷም ጉልላቷም ክርስቶስ እንደሆነ አምና ስለምትሰራው ህንፃ ቤተ-ክርስቲያን ልናገር? ወይንስ ስለ የትኛው ልናገር? ስለ ሰጎኑ እንቁላል? ከሰገነቱ በታች ስላለው መሶበ-ወርቅ? በክርስቶስ ልደት ወቅት ሄሮድስ ያስጨፈጨፋቸውን ሰማእት ህፃናትን ጩኅት ስለሚያዘክረው በጣርያው ዙሪያ ስላሉት ትናንሽ ቃጭሎች ባወራ ይሻል ይሆን? ስለ በሩና ስለ መስኮቱ ? ስለ ቤተልሄም? ስለ ቅድስተ ቅዱሳን? ወይንስ ስጋወ ደሙ ስለሚከብርበት ታቦቱ ልናገርን? እንዲህ ስርአቷ በሙሉ ባለሙያ ሴት በጥንቃቄ እንዳሰናዳችው ማእድ በአግባቡ ተሰናድቶ አንዱ ካንዱ ጋር ሳይጋጭ ፣ አንዱ አንዱን ሳያጠፋው ፤ ከመሰረቷ እስከ ጉልላቷ በወንጌል ባሽበረቀችው ቤተ-ክርስቲያን ላይ ክርስቶስንና የክርስቶስን መለኮታዊ ፈቃድ የሚቃወም ምን ነገር አገኛችሁና እናድስ ብላችሁ ተነሳችሁ? ይህስ የቤተ-ክርስቲያን ውበት ምእመናን እንደ ቤተ-ክርስቲያናቸው ስጋቸው ነፍሳቸውና ልቦናቸው እንዲሁ በወንጌል እያሽበረቀ ለአለም ሁሉ ክርስቶስን በህይወት እንዲሰብኩ የሚያነሳሳ መሆኑን ልብ አላላችሁም? ወይንስ እናንተ ዲያቢሎስን ያስከፋውን ይህን እፁብ ድንቅ የቤተ-ክርስቲያን ጌጥ ታፈርሱ ዘንድ ሰልፋችሁን ከሚጠፉት ጋር አደረጋችሁ? እንዲህስ ካልሆነ የትኛውን ታድሱ ዘንድ ፈለጋችሁ? በቅዱሳን ስም በየወሩ የሚዘከረውን ዝክር ከወንጌል ውጭ ነው ትላላችሁን? ምእመናንስ የሰንበቴውን በረከት ሊካፈሉ ሲሰባሰቡ ስትመለከቱ ትናደዳላችሁ? ወይንስ በክርስቲያኖች ቤት ዘወትር በልደታ የሚቀቀለውን ንፍሮ ትርጉሙ ቢጠፋባችሁ መሳለቅ ወደዳችሁን? እናንተ ለፀሎት ለፆምና ለምስጋና መንፈሳዊነታችሁ ቢደክም ፣ አለማዊ ደስታና ጥጋብ በእናንተ ላይ ቢሰለጥን ፣ የስጋዊ ሃብት ምቾት ከተጋድሎ ቢያስቀራችሁ ፤ ቅዳሴ ያጥር ዘንድ እንደ አዋቂ ትማከራላችሁን? ወይንስ ከ7ቱ አፅዋማት እየመረጣችሁ ይህንን ፁሙ ፣ ይህ እንኳን አይጠቅምም ለማለት እንዴት ትደፍራላችሁ?
እናንተ ተዋህዶን ልታድሱ የተነሳችሁ ፦የሆነ ሆኖ ከቀደሙት ቅዱሳን አባቶቻችን አብልጠን እናንተን እንሰማ ዘንድ የተገባ ይመስላችኅል? ቅዱስ ያሬድ ያከበራትን ፣ የኖረባትን ፣ ያፀናትን እምነት ትተን አላፊ ጠፊ በሆነው በዚህ አለም ወሬያችሁ ተታለን የምንወጣ እንደሆን ታስባላችሁ? ወይንስ አባታችን አቡነ ትክለሃይማኖት ህይወታቸውን በሙሉ በስርአቷ የተመላለሱባትን ፣ ቅዳሴዋን አስቀድሰው የቀደሱባትን ፣ የእጣኑን ሽታ አሽትተው እጣን ያጠኑባትን ፣ ጥምቀቷን ተጠምቀው ያጠመቁባትን ፣ ትምህርቷን ተምረው ያስተማሩባትን ፣ ከአለማዊ ግብር ተለይተው እንደ ተዋህዶ ስርአት በገዳም ራሳቸውን ወስነው በፆም በፀሎትና በተጋድሎ ከክርስቶስ ጋር የተገናኙባትን መሰላል ትተን በገንዘብ ፍቅር የወደቃችሁትን ፣ በአለም ወዳሴ ያበዳችሁትን ፣ ከፆም ከፀሎት የተለያችሁትን እናንተን እንሰማ ዘንድ የምንፋጠን ሞኞች መሰልናችሁን? እናንተስ በየትኛው መልካም መንፈሳዊ ፍሬያችሁ ከአባቶቻችን ጋር ትደመሩ ዘንድ አዲስንም ትምህርት ታመጡ ዘንድ ቻላችሁ? ከመጀመሪያወቹ የክርስትና መናንያን ቀዳሚ የሆኑት የተወደዱት አባ ጳውሊ ፦ ከ90 አመታት በላይ አንድን ሰው እንኳን ሳያዩ በፆም በፀሎት ተወስነው በሚኖሩ ጊዜ ፤ አባታችን አባ እንጦንስ በእግዚአብሄር ተመርተው አባ ጳውሊን ሊጎበኙ ቢመጡ ምስጉን የሆኑ አባ ጳውሊ አባ እንጦንስን አንድን ነገር እንዲያመጡላቸው ግድ አሏቸው ፤ ይሔውም አቡነ አትናቴዮስ የኦርቶዶክስ እምነትን በ318ቱ ሊቃውንት ህግ ካፀና በኅላ ለመነኮሳት ልብስ የሚሆን ስለአዘጋጀ ከዚህ የመነኮሳት ልብስ አንድ እንዲያመጡላቸው ነበር ፤ ይህንም የሚያደርጉት አትናትዮስ ያፀናትን የኦርቶዶክስ እምነትን ህይወታቸውን ሙሉ እንደያዙ መኖራቸውን ህዝቡ ሁሉ እንዲያውቅ ለምስክርነትም እንዲሆን ተናገሩ፡፡ ታዲያ እናንተ ኦርቶዶክስን ታድሱና ትቀይሩ ዘንድ የተነሳችሁ ከእነኘህ ፅኑ ፣ ቅዱስ ፣ ክርስቶስን የመሰሉ የምድር መላእክት ከሆኑ ስለ ወንጌልም ሁሉን ትተው ክርስቶስን ከተከተሉት አባቶች ትበልጡ ዘንድ ተገባችሁን? እንግዲህስ እወቁት እኛስ እናንተ በምትነግሩን ነፍስንም ደስ የማያሰኝ አዲስ እውቀት በመንግስተ ሰማያት ከምንኖር ይልቅ እነ አባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ ፣ እነ ቅዱስ ያሬድ ፣ እነ ቅዱስ ዮሃንስ አፈወርቅ ፣ እነ ቅዱስ ጊዮርጊስ ፣ እነ አቡነ ተክለሃይማኖት የነገሩንን ይዘን ፣ የኖሩበትን ህይወት ኖረን ሲኦል እንድንገባ እንመርጣለን፡፡ ነገር ግን መንግስተ ሰማያት ለእንደዚህ ያሉ ቅዱሳን አባቶች የተዘጋጀች እንደሆነች የክርስቶስ ወንጌል ይመሰክራል ፤ ይህችም ቅድስት ቦታ አለምን ንቀው ፣ ርቀው ፣ ጠልተው በእግዚአብሄር ትእዛዝ ለሚፀኑት እንደተሰጠች ፣ የመንፈስ ቅዱስ ፀጋም በፀሎት ፣ በፆም ፣ ትሩፋትን አብዝቶ በመስራትና በመሳሰሉት መንፈሳዊ ተግባራት የሚገኝ እንደሆነ እናውቃለን፡፡
እኛም ክብር የሚገባው ኢየሱስ ክርስቶስ የበግ ለምድ ለብሰው ከሚመጡ በውስጣቸው ግን ነጣቂወች ተኩላወች ከሆኑ ተጠበቁ ፤ እንዚህንም ከፍሬያቸው ትለዩዋቸዋላችሁ እንዳለን ፤ ወንጌል በሚያበራልን ብርሃን ተኩላወችን ነቅሰን እናወጣ ዘንድ ይገባናል፡፡ እናንተም ተዋህዶን ታድሱ ዘንድ የተነሳችሁ ለሰው ሁሉ የሚታየው ፍሬያችሁ መልካም አይደለምና አስቀድማችሁ ራሳችሁን በንስሃ ታድሱ ዘንድ አይሻላችሁምን? ስለ ገንዘብም ያላችሁን መገዛትና መመካት ትተው ዘንድ የተገባ ነው፡፡እናንተ ግን መንፈሳዊ ሰው የመንፈስን ስራ በገንዘብ እንዳይለውጥ አባቶቻችን ሃዋርያት መንፈስ ቅዱስን የማሳደር ፀጋን በፈቀደው ሰው ላይ ለማውረድ እንዲችል ከሃዋርያት ጋር ፀጋውን በገንዘብ ሊደራደር የሞከረውን ከንቱ ሰው የዘለፉበትን ነገር እረሳችሁት፡፡”የሚያበራየውን በሬ አፉን አትሰሩት” የሚለውን የአምላክ ትእዛዝ እንደገዛ ፈቃዳችሁ ለሆዳችሁ እንዲስማማ አድርጋችሁ ተረጎማችሁት፡፡የክርስቶስን ወንጌልና የመንፈሳዊውን ስራ በገንዘብ የመሽጣችሁን ነገር “ለሰራተኛ ደመወዙ ይገባዋል” በሚለው እድሜያችሁን ሙሉ የማትጨርሱትን ምድራዊ ሃብትን ማከማቻ አደረጋችሁት፡፡ የኦርቶዶክስ መንፈሳዊ አባቶቻችን ግን እጅግ ውድ የሆነውን መንፈሳዊውን ፀጋ እጅግ ርካሽ ለሆነው አለማዊ ንዋይ እንዳይለውጡትና ከንቱ በሆነው ግብር እንዳይተባበሩ ከህሊናቸውና ከዚህ አለም አምሮት ጋር እድሜያቸውን ሙሉ ታገሉ ፤ ስላሽነፉትም ለክርስቲያን ወገኖች ሁሉ ትምክህትና አርአያ ተባሉ፡፡እናንተ ግን ከዚህ አለም ናችሁና የአለም ምኞቷና አምሮቷ ጠልፎ ጣላችሁ፡፡ መንፈሳዊ ከመባልም የለየለት አለማዊ ነጋዴ ወጣችሁ፡፡ ስለነጋዴነታችሁም መንፈሳዊውን ስብከትም ሆነ መዝሙር ስታዘጋጁ የመንፈሳዊው ጌታ እግዚአብሄር ምን ብናገር ይወዳል(what God want or what the people need) ከማለት ይልቅ የዚህ ስብከትና መዝሙር ገዥ ምን ባዘጋጅለት ብሩን ደስ ብሎት ያወጣል ( what the people want) በሚል ለወጣችሁ፡፡በዚህም እግዚአብሄርን ማገልገል ትታችሁ ስለ ገንዘብ ጥማት የሰይጣንና የሰው ባርያ ሆናችሁ፡፡ በአለማዊውም ምቾትና መንደላቀቅ በሚገኝ በሚስረቀረቅና በሚያስገመግም ድምፅ ፣ ስለ ሃጢአት ሰውን ከመገሰፅ ይልቅ ፃድቅ በማድረግ ፣ በትህትና ራስን ዝቅ ከማድረግ ፈንታ በትእቢት ከሁሉ በላይ ራስን መስበክና ማስወደድን በማብዛት መልካም የነበረውን ሰው አለማዊ በሆነው ተግባራችሁ ከመንፈሳዊ ስነምግባር ይወጣ ዘንድ ታፋጥኑታላችሁ፡፡እንግዲህ እኔ ደግሞ የእናንተን ሃጢአት ስዘረዝር ራሴን ፃድቅ ማድረጌ ነውን?አይደለም ፤ የእናቴን ቤት አጥር ልታፈርሱ ስትነቀንቁ ስላየኅችሁ እንጂ ፡፡ታዲያ እስኪ ንገሩን ፦ የትኛው መልካም ስራችሁ ተዋህዶን ልታድሷት አደረሳችሁ?
ለመሆኑ ተዋህዶን ታድሷት ዘንድ የተነሳችሁ እናንተ እነማን ናችሁ? የክርስቶስን ወንጌል ለመስበክ ቤተ-ክርስቲያን ከምትችለው በላይ ለዚያውም የታወቀ አለማዊ መምህር ከሚጠይቀው ገንዘብ የሚበልጥ ካልተከፈለን ወንጌልን አንሰብክም የምትሉ ብኩኖች ፤ እኛም ካልሰበክን ጉባኤው ይፈታል የምትሉ ትእቢተኞች ስትሆኑ ፦ ከአለም ኑሮ ፣ መንፈሳዊ ኑሮ እንዲበልጥ ፤ ከገንዘብ ፍቅር የእግዚአብሄር ፍቅር እንዲሻል እንዴት መናገር ትችላላችሁ? ወይንስ በተገኘው አጋጣሚ ሁሉ ባከማቻችሁት የደሃ ገንዘብ ፤ እናንተ እያማረባችሁ ፣ እየወዛችሁ ፣ እየወፈራችሁ ና ትካሻችሁ እያበጠ ስትታዩ የምትሰብኩት ምእመናን ደግሞ እየጎሰቆሉ ፣ እየገረጡና እየከሱ መምጣታቸው መልካም እረኛ የሚያደርጋችሁ ይመስላችኅል? የተዋህዶ እውነተኛ እረኞች ግን ክርስቶስ እንዳደረገ በጎቹ እንዳይባዝኑበት ራሱን መስዋእት ያደርጋል፡፡ ዛሬ ዛሬ የተዋህዶ እውነተኛ እረኞች ከአንዱ ሃገር ወደ ሌላው ፣ ካንዱ መምህር ወደ እዚያኛው እየተንከራተቱ የክርስቶስን ወንጌል አምልተው ፣ አመስጥረው ቅኔን ፣ ዜማን ፣ ትርጓሜን ፣ አቋቋምን እድሜ ልክ ተምረው ሊቀ ሊቃውንት ቢባሉ ፦ ተራራ ለተራራ ፣ ዋሻ ለዋሻ ፣ ገጠር ለገጠር እየዞሩ ገዳማቱ እንዳይፈቱ ፣ የአብነት ትምህርት ቤቶች እንዳይበተኑ ፣ ምእመናን ከምግባር ከሃይማኖት እንዳይርቁ በ 40 ና በ 80 ብር ቤተ-ክርስቲያናቸውን ደከመኝ ሰለቸኝ ሳይሉ ሲያገለግሉ ፤ እናንተ ግን ምን ፣ መቼና የት እንደተማራችሁ እንኳን በቅጡ የማይታወቅ በሚልዮን የሚቆጠር ገንዘብን በቤተ - ክርስቲያን ስም ስታስገቡ ከእግዚአብሄር ይልቅ ለገንዘብ መገዛታችሁ እንደሆነ አታውቁምን? ወይንስ የገንዘብ ፍቅር መልካም ስራን ሁሉ እንደሚያጠፋ አልተማራችሁም? ወይንስ ደመወዛችሁ ይብቃችሁ የተባሉትን እውነተኛ የተዋህዶ ሊቃውንት የክርስቶስን ወንጌል በገንዘብ እንዲቀይሩ ፈተና እንደሆናችሁባቸው አልተረዳችሁምን?
ፕሮቴስታንታዊ በሆነው ስብከታችሁና መዝሙራችሁ ደግሞ የቅዱሳንን በትህትና ዝቅ ማድረግ እንደ ውርደት ቆጥራችሁ ራሳችሁን በሰውና በአምላክ ፊት ከፍ ከፍ ስታደርጉና ራሳችሁን ስታፀድቁ ፤ ተዋህዶ ግን ስለቅዱሳን መናገር አንድም ህይወታቸው ትምህርት ስለሆነ አንድም በረከታቸውን ለመካፈል እንደሚረዳ ስታስተምር ፣ እናንተ ግን የቀደሙ ቅዱሳን አባቶችን ማስረሳትን አንድም ምእመናንን ከበረታቸው ለማስወጣት አንድም በቀደሙት አባቶች መልካም ተጋድሎ የእናንተ ስራ እንዳይጋለጥ ስራየ ብላችሁ ተያያዛችሁት፡፡እናንተ ሌባ ሌባነቱ ቢታወቅ ፈቃዱን ይፈፅም ዘንድ ስለማይችል ፣ አመቺ ጊዜ እስኪያገኝ መልካም ሰው መስሎ ለመታየት ጥረት እንደሚያደርግ ፤ እናንተም አላማችሁን ሳታሳኩ ተሃድሶነታችሁ እንዳይጋለጥ በመዝሙራችሁና በስብከታችሁ ውስጥ በጥቂቱ ስለ አምላክ እናት ከመናገር ያለፈ እስኪ ስለ ሰማእቱ ጊዮርጊስ ፣ ሰማእቱ እስጢፋኖስ ፣ አቡነ ዘርአ ብሩክ ፣ አቡነ አረጋዊ ፣ አቡነ ሃብተ ማርያም ፣ ቅድስት አርሴማ ፣ ቅድስት ክርስቶስ ሰምራ፣ስለ ቅዱሳን መላእክት ፣ ስለ ሌሎችም ቅዱሳን ሁሉ በስህተት እንኳን የት ቦታ አስተማራችሁ? ነገር ግን ተዋህዶ እግዚአብሄር በቅዱሳኑ ድንቅ ነው የሚለውን ታምናለች ታስተምራለችም፡፡ ይህንንም የየወሩን እለታት በስማቸው ለመታሰቢያቸው ሰጥታ ትዘክራቸዋለች፡፡ እናንተ ግን ልጆቿ አይደላችሁምና ከእርሷ ያልሆነ አዲስን ዘር ትዘራላችሁ፡፡ እስኪ ንገሩን ፦ ቅዱስ ጳውሎስ እኔ ክርስቶስን እንደመሰልኩ እኔን ምሰሉ እንዳለ እነዚህን ቅዱሳን እንደታዘዝን የኑሯቸውን ፍሬ እያየን በእምነት እንመስላቸው ዘንድ ካልቻልን መንፈሳዊነትን ከማን እንማር ዘንድ ትወድዳላችሁ? ከእናንተ እንማር ዘንድ ፈቃድ ካላችሁስ ህይወታችሁን አይተን እንማርበት ዘንድ መልካሙ ፍሬያችሁ የት አለ? ወይንስ እውር እውርን ይመራው ዘንድ ይችላልን? እንደዚያስ ከሆነ መንፈሳዊ አይን በተለየው ህይወታችሁ የተዋህዶን ህፀፅ እንዴት ልትመለከቱ ቻላችሁ? ወይንስ ስለ ፆም ስለ ፀሎት መስማታችንን ትተን የእናንተ ችሎታ ስለሆነው በክርስቶስ ወንጌል እንዴት ገንዘብ መስራት ይቻላል? የሚለውን እናጥና ይሆን? ወይንስ ራስን በማክበድና በማስወደድ እንዴት የሰውን ከበሬታ ማገኘት እንደሚቻል እንማር? እኛስ ይህንን የሰይጣን ስራ እንዳንሰራ ፣ ሲጀመርም እናንተን እንዳንሰማ ፣ ከተኩላወችም ጋር እንዳንተባበር ክርስቶስ አስቀድሞ አዘዘን፡፡
ፕሮቴስታንታዊ በሆነው ስብከታችሁና መዝሙራችሁ ነፍስ የተለየው ስጋ ምውት እንደሆነ ከስራም የተለየ እምነት ባዶ ነው የሚለውን የተዋህዶ አስተምሮ ትታችሁ ለአለማዊ አኗኗር የሚስማማውን ስራ ስለተለየው እምነት አብዝታችሁ ታስተምሩ ዘንድ ደከማችሁ፡፡ነገር ግን ተዋህዶ ወርቅ ወርቅነቱ በእሳት ተፈትኖ እንዲታወቅ እምነትም ከዚህ አብልጦ በስራ እንዲፈተን ለልጆቿ ታስተምራለች፡፡ይህን የሚያውቁ ልጆቿም ዘወትር ለትሩፋት ይፋጠናሉ፡፡ነገር ግን እናንተ ፍሬ የማያፈራ ፣ ክብር የሚገባው አብም ያልተከለው የሚነቀል ዘርን በአሽዋ ላይ ትዘሩ ዘንድ ሮጣችሁ፡፡ፕሮቴስታንታዊ በሆነው እምነታችሁ በገዳም ተወስኖ እድሜን መጨረስ የሰነፎች ስራ ነው በማለት የአባ እንጦንስንና የአባ መቃርስን ትምህርት ሻራችሁ፡፡ነገር ግን በሰው ተከቦ ለአለም ሁሉ ወንጌልን ከመስበክ ፣ ተአምራትንም እያደረጉ ዋጋን ከሰው ከመቀበል ፤ ራስን ስለ ክርስቶስ ከሰው ለይቶ ፣ ከምቾት ርቆ ፣ ስጋን ለነፍስ አስገዝቶ ፣ አብዝቶ በመፆም ፣ አብዝቶ በመፀለይ ፣ የሌሊቱን ድምፀ አራዊት ታግሶ ፣ የሰይጣንን ድብቅና ግልፅ ፈተና ታግሎ ድል ማድረግ ምን ያክል አድካሚና ዋጋውም የቱን ያክል የበዛ እንደሆነ ዘነጋችሁ፡፡ እናንተ ግን ለስጋችሁ አምሮት ከዚህ ግርግር ከበዛበት አለም የተሻለ አታገኙምና ለገዛ ምቾታችሁ የእግዚአብሄርን ፈቃድ ትቃወማላችሁ፡፡ ታዲያ እስኪ ንገሩን ፦ በሁሉ ስህተት ሆናችሁ እያየን እናንተን እንሰማ ዘንድ የሚገባ ይመስላችኅል?
እንግዲህ የተወደደው አባት አባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ ኖሮበት ያለፈውን የቤተ-ክርስቲያናችን ዶግማና ቀኖና ይታደስ ዘንድ የምትሮጡ እናንተ እነማን ናችሁ? ወይንስ ማደስ (renew) የሚለውን ቃል መቀየር (change) ወይም ማሻሻል (upgrade) አድርጋችሁ ወሰዳችሁን? ማደስ ማለት ወደ ድሮው ወይም ወደቀደመው ነገር መመለስ (back to the Origional) እንደሆነ አላስተዋላችሁምን? ኦርቶዶክስን እናድሳት ስትሉስ ወደቀደመው ስርአቷ እንመልሳት ማለት እንደሆነ ካወቃችሁ ከቀደሙት ቅዱሳን አባቶች የተሻለ የቀደመችውን ሃይማኖት ታውቁ ዘንድ እንዴት ቻላችሁ? ነገር ግን የሰይጣን ምክር እንዳይዘነጋ የእናንተም ሃሳብ መልካም ስራን መስራት ሳይሆን አውሮፓውያንና አሜሪካውያን የራሳቸውን ህዝብ ከሃይማኖተኛነት አውጥተው አለማዊ አድርገውት ሲያበቁ ፦አሁን ደግሞ በሃይማኖት የፀኑትን የኦርቶዶክስ አማኝ ክርስቲያኖች ወደ አለማዊነት ወደሚያንደረድረው የፕሮቴስታንታዊ ምንፍቅና ማሰደድ ነው፡፡ ነገር ግን ቤተ-ክርስቲያን በክርስቶስ አለትነት ላይ የተመሰረተች ናትና የገሃነም ደጆች እንኳን አይችሏትም፡፡ እኛም ከቀደሙት ቅዱሳን አባቶች ይልቅ እናንተን ፤ ከመልካሙ መንፈሳዊ የህይወት ፍሬ ይልቅ የከረፋውን አለማዊ ህይወታችሁን አይተን እንታለል ዘንድ እንዳንችል እናንተ የናቃችኅቸው የቅዱሳን ፀሎት ዘወትር ይጠብቀናል ፡፡
እንግዲህ ምን እንላለን ፦ እንዚያ አምነው የነበሩ የካዱትንም ትመልሷቸው ዘንድ አትድከሙ የሚለውን የተወደደ የሃዋርያ መልእክት እንሰማ ዘንድ ይገባናል፡፡ እናንተ ግን መልካችሁን እንደ ዲያቢሎስ እየቀያየራችሁ መኖሩ ልብንና ኩላሊትን በሚመረምር በእግዚአብሄር ዘንድ የተጠላ መሆኑን አስተውሉና ለነፍሳችሁ እዘኑላት፡፡ እኛ ልክ ነን ካላችሁ ግን ውጡ ፤ እምነታችሁን ይዛችሁ እምነታችንን ልቀቁልን፡፡ ስለ እምነታችሁም በአደባባይ ስበኩ ፣ አውሩ ፣ አስተምሩ ፤ ነገር ግን የተዋህዶ ቤተ-ክርስቲያን አውደ ምህረት የእናንተ አይደለምና ውረዱ ፡፡ እግዚአብሄርም በውሽት ፣ በማጭበርበርና በማስመሰል እንደማይከብር ፣ በዚህም ሰወች ወደእርሱ ይመጡለት ዘንድ እንደማይፈልግ እወቁ፡፡ እናንተም ከእኛ ወገን የሆናችሁ ባለማወቅም ፣ በስንፍናም ከእነዚህ ጋር የምትተባበሩ የተዋህዶ ልጆች ስለ እናታችን ስለ ቅድስተ ቅዱሳን ድንግል ማርያም ብላችሁ ከፀረ-ተዋህዶ የዲያቢሎስ ተላላኪወች ተለዩ፡፡እናንተ ግን ተዋህዶን ልታድሱ የተነሳችሁ ፦ ከቀደሙት ቅዱሳን አባቶቻችን አብልጠን እናንተን እንሰማ ዘንድ የተገባ ይመስላችኅል? ወይንስ ቅዱስ ያሬድ ያከበራትን ፣ የኖረባትን ፣ ያፀናትን እምነት ትተን አላፊ ጠፊ በሆነው በዚህ አለም ወሬያችሁ ተታለን የምንወጣ እንደሆን ታስባላችሁ?
ወስብሃት ለእግዚአብሄር ፣ ወ ለወላዲቱ ድንግል ፣ ወ ለመስቀሉ ክቡር፡፡